የልማታዊ ባለሀብቶቻችን አያያዝ ቢፈተሽ

የአምራች ኢንዱስትሪውን ዘርፍ ለማሳደግ የአገር ውስጥ ባለኃብቱን ተሳትፎ የማጎልበት ስራ በመንግስት በኩል እየተሰራ መሆኑ ይታወቃል። ይህ ስራ አገሪቱንም፤ ባለሃብቱንም በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ ተጠቃሚ ለማድረግ በሚያስችል አኳኋን እየተከናወነ ቢሆንም እድገቱ የሚፈለገውን ያህል አለመሆኑን ዘርፉን የተመለከቱ ተቋማት እየገለጹ ነው። በተለይም አብዛኞቹ ወደ ውጭ የሚላኩ የግብርና ምርቶች እሴት ሳይጨመርባቸው ስለሚላኩ አገሪቱ ማግኘት የሚገባትን ጥቅም ማግኘት አልቻለችም።

በመሆኑም በአምራች ኢንዱስትሪው ዘርፍ  የባለኃብቱን ተሳትፎ በማሳደግ በአንድ በኩል አገሪቱ በሌላ በኩል ደግሞ ባለኃብቶቹ ተጠቃሚ መሆን እንዲችሉ በመንግስት በኩል የማምረቻ ቦታዎች፣ የብድር አገልግሎት፣ የአቅም ግንባታ ድጋፎች እየተሰጡ መሆናቸውን የሚጠቁሙት መረጃዎች የገበያ ትስስር እንዲፈጥሩም ትኩረት እየተደረገ መሆኑን አመልክተዋል።

የአገር ውስጥ ባለኃብቶች በተቀናጀ የቡና፣ የሰሊጥ፣ የበቆሎ ማቀነባበሪያ ፋብሪካ እንዲሁም በቆዳ ምርት፣ በጨርቃጨርቅ፣ በወረቀት ምርቶች ግብዓት ማምረት ላይ ቢሰማሩ ውጤታማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ነው በርካታ መረጃዎች እያመለከቱ የሚገኙት። ጥቂቶቹን እንመልከት።

በዘርፉ የሚሳተፉትን ኢንተርፕራይዞች ለማበረታታት የኢትዮጵያ ልማት ባንክ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ከ41 ቢሊዮን ብር በላይ መድቦ በመላ አገሪቱ 110 ቅርንጫፎችን በመክፈት እየተንቀሳቀሰ ነው። በሌሎች በተመረጡ ዘርፎች ላይ ከ500 ሺህ እስከ 7 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ካፒታል ላላቸውና ከስድስት በላይ ሠራተኛ ላላቸው ኢንተርፕራይዞች በልማት ባንክ በኩል የካፒታል እቃዎች ኪራይና የዱቤ ግዥ አገልግሎት እንዲሁም 75 በመቶ የብድር ድጋፍ ተዘጋጅቷል።

ዘጠኝ መሰረታዊ አቅጣጫዎችን የያዘው ሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ማስፈፀሚያ 2 ነጥብ 3 ትሪሊዮን ብር ወጪ ይጠይቃል። ወደ ውጭ ምንዛሪ ሲቀየር ደግሞ 106 ነጥብ 9 ቢሊዮን ዶላር ነው።

በእቅዱ ዘመን የውጭ ምንዛሪ ፍላጎታችን 119 ነጠብ 5 ቢሊዮን ዶላር ሲሆን 115 ቢሊዮን ዶላር ገቢ የሚጠበቅ መሆኑን የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት በእቅድ ዘመኑ መጀመሪያ ላይ ይፋ ያደረገው መረጃ ያመለክታል። የሌሎቹን ዘርፎች ትተን አጀንዳችን ወደሆነው የአምራች ኢንዱስትሪው በመሻገር የጽ/ቤቱን መረጃዎች እንመልከት።

በእቅድ ዘመኑ አምራች ኢንዱስትሪው 3 ነጥብ 6 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ያመነጫል ተብሎ የሚጠበቅ እንደሆነ የሚጠቁመው ይህ መረጃ፤ በሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ዘመን ሰባት ሚሊዮን ካሬ ሜትር ስፋት ያለው የኢንዱስትሪ ፓርክ ይለማል ይላል። (እስከ አሁን ድረስ አዲስ የኢንዱስትሪ መንደር፣ ቦሌ ለሚና ሀዋሳ የኢንዱስትሪ ፓርኮች  ተጠናቅቀዋል)።

የድሬዳዋ፣ ኮምቦልቻ፣ መቀሌ፣ አዳማ፣ ባህርዳር፣ ቦሌ ለሚ 2፣ ቂሊንጦና ጅማ የኢንዱስትሪ መንደሮች በግንባታ ሂደት ላይ ሲሆኑ፤ ከማዕድን ዘርፍ 570 ነጥብ 4 ሚሊዮን ዶላር የውጭ ምንዛሪ ገቢ ይገኛል ተብሎ ይጠበቃል ። 5 የባዮ ኢታኖል ማምረቻና 6 የባዮ ዲዝል ማምረቻ ፋብሪካዎችም ይገነባሉ ።

በአምስት ዓመታት ውስጥ የግል ኢንቨስትመንት ከ262 ቢሊዮን ወደ 740 ቢሊዮን ብር እንዲያድግ ይደረጋል። 624 ቢሊዮን ብር የአገር ውስጥ ባለሃብቶች ድርሻ ሲሆን ቀሪው የውጭ ባለሃብቶች መሆኑን ቢጠቁምም፤ አሁን የእቅድ ዘመኑ በከፊል እየተጠናቀቀ በሚገኝበት ወቅት ላይ የሃገር ውስጥ ባለሃብቱ ተሳትፎ እዚህ ግባ የማይባል መሆኑ ነገሩን ግራ አጋቢ አድርጎታል። ለዚሁ ዘርፍ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ድጋፋቸው የጎላ የሚሆኑ ዘርፎችንም በተመለከተ ጽ/ቤቱ ይፋ ባደረገው መረጃ በግልጽ ተመልክቷል።

ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች በእቅድ ዘመኑ ለ8 ነጥብ 5 ሚሊዮን ሰዎች የስራ ዕድል እንዲፈጥሩ ይደረጋል። አጠቃላይ የመንገድ ሽፋናችንም ከ120 ሺህ ወደ 220 ሺህ ኪሎ ሜትር የማሳደግ ግብ ተቀምጦ እየተሰራ ነው። 2ሺህ 782 ኪሎ ሜትር የባቡር መስመር ግንባታና 2ሺህ 741 ኪሎ ሜትር ብሄራዊ የባቡር መስመር ኔትወርክ ስራ በማካሄድ የትራንስፖርት ወጪን በከፍተኛ ሁኔታ ለመቀነስና ትስስሩን ለማሻሻል እቅድ ተይዞ በመከናወን ላይ ይገኛል።

በአየር ትራንስፖርት ዘርፍ የአውሮፕላኖችን ቁጥር ወደ 113 በማድረስና ዓመታዊ መንገደኞችን የማጓጓዝ አቅም ከ5 ሚሊዮን ወደ  18 ሚሊዮን በማሳደግ እንዲሁም የካርጎ አገልግሎቱን ወደ 503ሺህ 700 ቶን  ከፍ በማድረግ  በእቅድ ዘመኑ መጨረሻ 5 ነጥብ 1 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር እንዲያመነጭ የሚደረግ መሆኑ ተመልክቷል ።

የሞባይል ተጠቃሚዎች ቁጥር ከ38 ሚሊዮን ወደ 103 ሚሊዮን፣ የብሮድባንድ ኢንተርኔት ዳታ ተጠቃሚዎች ቁጥር 39 ሚሊዮን በማድረስና ሌሎች አገልግሎቶችም ጭምር በማስፋፋት በተለይም የሞባይል ሽፋን 81 በመቶ ለማድረስ ታቅዷል፤ ብሄራዊ የውሃ አቅርቦት ሽፋኑን ከ58 በመቶ ወደ 83 በመቶ ከፍ የማድረግ ግብም ተቀምጧል ።

ምንም እንኳን እቅዱ የአምስት ዓመት ቢሆንም ሁለቱ ዓመታት ተጠናቅቀዋል። የሁለቱ ዓመታት ጉዞአችን የሚያመላክተው ደግሞ ከላይ የተመለከቱት ማበረታቻዎች ቢኖሩም የሃገር ውስጥ ባለሃብቱ ተሳትፎ ዘገምተኛ መሆኑን ነው። በሂደቱ የተሳኩትንና  ያልተነኩትን ለይቶ ስለምንነታቸውን መፈተሽ ያስፈልጋል።  

መንግሥት አገሪቱ ለኢንቨስትመንት ምቹ መሆኗን በማረጋገጥ የተለያዩ ድጋፎችንና ማበረታቻዎችን በመስጠት ከውጭ ኢንቨስተሮች ባሻገር በተለይ ለሃገር ውስጥ ባለሃብቱ ጫን ያሉ ማበረታቻዎች በማድረግ ወደዘርፉ ለመሳብ ጥረት ቢያደርግም ጉዞው የኋልዮሽ ከሆነባቸው ምክንያቶች አንዱና ዋነኛው ኢንቨስትመንቱን የሚያዳክሙ የህግ ጥሰቶች መፈጸማቸው ስለመሆኑ ብዙዎቹ ይስማማሉ። 

የውጭም ሆነ የአገር ውስጥ ኢንቨስተር መስተናገድ ያለበት በሕጉ መሠረት ብቻ ነው፡፡ በዚሁ አግባብ ሕጉ ለኢንቨስትመንት የማይመቹ ክፍተቶች ካሉበት እነሱን ማስተካከል ይገባል፡፡ ሕጉ የተሟላ ሲሆን ለአፈጻጸም አያስቸግርም፡፡ ከጎረቤት ጀምሮ የተለያዩ የአፍሪካ አገሮች የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት ለመሳብ ጠብ እርግፍ በሚሉበት በዚህ ዘመን፣ ኢንቨስተሮችን የሚያበሳጩ ድርጊቶችን መፈጸም ተገቢ አይደለም።  

በእርግጥ የውጭ ኢንቨስተሮች ቀልጣፋ የባንክ አገልግሎት፣ አስተማማኝ የኤሌክትሪክ ኃይል፣  የመንገድ መሠረተ ልማት፣ የትራንስፖርት አገልግሎት፣ ፈጣን የጉምሩክ ሥነ ሥርዓት፣ ከሙስና የፀዳ ቢሮክራሲ፣ ሰላምና መረጋጋት፣ ወዘተ. እንደሚፈልጉት ሁሉ የሃገር ውስጦቹም ይፈልጋሉ፡፡ የውጭ ኢንቨስተሮቹ የመንግሥት ተቋማት ጠንካራና ዘመናዊ እንዲሆኑ በሚሹት ልክ የሃገር ውስጦቹም ይፈልጋሉ፡፡ በብልሹ አሠራሮች ምክንያት መንገላታት አይፈልጉም፡፡ በዚያ ላይ ደግሞ የሕግ የበላይነት እንዲኖር ይፈልጋሉ፡፡ ከዚህ አንጻር የውጮቹ ተሳትፎ እነዚህ ፍላጎቶች ሁሉ መሟላታቸውን የሚያጠይቅ ነው። ይህ ከሆነና የሃገር ውስጦቹም ሆነ የውጮቹ በተመሳሳይ ህግ ከተመሩና ይልቁንም ጫን የሚለው ማበረታቻ ለሃገር ውስጦቹ ከሆነ የሃገር ውስጦቹ ተሳትፎ እንደውጮቹ ያልሆነበት ምክንያት ምንድነው? የሚለውን መፈተሽና ምናልባትም አስፈጻሚው አካባቢ ፈረንጅ አምላኪነት ስር ሰዶ ከሆነ መፈተሽ ያስፈልጋል። የውጮቹ በእርግጥም ከላይ የተመለከቱት እና ለሃገር ውስጥም ባለሃብቶችም ተፈጻሚ እንዲሆኑ የተቀመጡ የህግ ማእቀፎች አግባብ እየሰሩ ለመሆኑ አንድ ሰሞንኛ እና የህግ ማእቀፉ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ መጠቀማቸውን እና መጠቀማችንን የሚያረጋግጥ የስኬት አብነት እዚህ ጋር እንመልከት።  

ኢትዮጵያ የሲሚንቶ ምርት ወደ ጎረቤት አገሮች በመላክ 14 ነጥብ 16 ሚሊየን ዶላር ማግኘቷን ያመለከተው የኬሚካልና ኮንስትራክሽን ግብዓት ኢንዱስትሪ ልማት ኢንስቲትዩት መረጃ ነው፡፡ ባሳለፍናቸው አስራ አንድ ወራት ምርቱ የተላከው ወደ ኬንያ፣ ሶማሊያና ጅቡቲ መሆኑን ያመለከተው ኢንስቲትዩቱ፤ በኢትዮጵያ ካሉት ሃያ ሲሚንቶ ፋብሪካዎች አንዱ የሆነው የዳንጎቴ ፋብሪካ ብቻውን በዓመት 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ቶን ሲሚንቶ የሚያመርት መሆኑን ይጠቅሳል፡፡ ይህ ደግሞ ከላይ ለተመለከተው ግራ ገብ ጥያቄ ሁነኛ መልስ የሚሰጥ ነው።

ይህ ብቻ አይደለም በአሁኑ ጊዜ ኢትዮጵያ ከዓለም ዙሪያ በሚመጡ የውጭ ኢንቨስተሮች እየተጠቅለቀለቀች መሆኑ የሚያሳየን ነገር ከላይ የተመለከቱት ማበረታቻዎች እና ፍላጎቶች በመሟላታቸው መሆኑ አያጠያይቅም። በሃገር ውስጥ ባለሃብቶች በኩል ደግሞ ለማመን የሚከብዱ ምሬቶች ይሰማሉ፡፡ ስለሆነም ለአገር ማሰብ ማለት የአገርን ዘለቄታዊ ጥቅም የሚያስከብር ተግባር ማከናወን ማለት እንደሆነ ህግን ተጻራሪ የሆኑ ፈረንጅ አምላኪዎች (ካሉ) ሃይ ሊባሉ ይገባል፡፡ ‹ኢትዮጵያ ለኢንቨስትመንት ምቹ ናት› በማለት መፈክር ከመደርደር ይልቅ፣ ለኢንቨስትመንት ፀር የሆኑ መሰናክሎችን ማስወገድ ይሻላል፡፡ በኢንቨስተሮች አካባቢ ችግሮች ቢፈጠሩ እንኳ ረጋ ባለ መንገድ በውይይት መፍታት ይቻላል፡፡ ግብታዊነት የተሞላባቸው ዕርምጃዎችን በመውሰድ ማጣፊያው እንዳያጥር፣ ሁሉንም ወገን የሚያግባባ የጋራ ውሳኔ ላይ መድረስ ይጠቅማል፡፡ ሕግ አስከብራለሁ የሚል አካል ከምንም ነገር በላይ አላስፈላጊ ድርጊቶች እንዳይፈጽሙ መከላከል በሚያስችል ቁመና ላይ የሚገኙ ሃይሎችን ብቻ ዘርፉ ላይ ማሰማራት ያስፈልጋል ፡፡

 

ለሕግ የበላይነት ትኩረት ሲነፈግ ሕገወጥ ድርጊቶች የበላይ ይሆናሉ፡፡ በዚህም ሳቢያ የመንግሥት አሠራር ግልጽነት አይኖረውም፡፡ ግልጽነት በሌለበት ደግሞ ተጠያቂነት አይኖርም፡፡ በደካማ መንግሥታዊ መዋቅሮች ውስጥ የተሸሸጉ ሙሰኞች ኢንቨስተሮችን አላሠራም ማለታቸው አይቀሬ ነው። የተሽመደመደው ቢሮክራሲም እንክትክቱ ሊወጣ ይገባል። ችግሮች ሲፈጠሩ እየተንቀረፈፈ ግራ የሚያጋባ ሳይሆን፣ በፍጥነት ምላሽ መስጠት የሚችል አሠራር መዘርጋትና ለዚሁ የሚመጥን ፈጻሚና አስፈጻሚ መሰየም ይገባል፤ ጊዜውም ግድ ይላል። እንዲበራከቱልን የምንሻቸውን ልማታዊ ባለሀብቶቻችንን እንዴት እያስተናገድናቸው፤ አያያዛችንስ ምን እንደሚመስል ቢፈተሽ፤ ቢመረመር መልካም ነው።