“እየታደስን እንሰራለን፤ እየሰራንም እንታደሳለን”

ሶፊስቶች ከአስተያየት በቀር ፍጹም እውነት በሰው ዘንድ የለም የሚሉ ፈላስፎች ናቸው፡፡ ሶቅራጥስ ግን የተጣራም ባይሆን በሰው ህሊና እና አዕምሮ ፍጽምና ያለው እውነት ሊኖር እንደሚችል የሚያምን ፈላስፋ ነው፡፡ ይህ እውነት ግልጥ ሆኖ እንዲወጣ፤ የሰዎችን ሐሳብ በትምህርት እና በአዕምሮ ምርመራ ማበልጸግ አስፈላጊ ነው ይላል፡፡ እንደርሱ አስተሳሰብ፤ ‹‹የዕውቀት መነሻ እና መድረሻ፤ ርትዕ፣ ፍትሕ እና በጎ ምግባር ናቸው፡፡››

ሆኖም የሶቅራጥስን ሐሳብ የሚቃወሙ በርካቶች ነበሩ፡፡ እናም በመሰሪዎች ክስ ተመስርቶበት ፍርድ ቤት ቆሞ የሞት ፍርድ ተፈረደበት፡፡ ፍርዱ በተፈረደ ጊዜ አፖሎ ለሚባለው የጣዖት አምልኮ የሚደረግ ዓመታዊ በዓል ይደረግ ነበር፡፡ በዓሉ የሚከበረው ዲሎስ በተባለች ደሴት ሲሆን ለክብረ በዓሉ ከአቴና ሰዎች ይላኩ ነበር፡፡ እናም እንዲህ ያለው መንፈሳዊ ጉዳይ በሚከበርብበት ጊዜ የሞት ፍርድ እንዳይፈጸም ህጉ ይከለክል ስለነበር ከአቴና መልዕክተኞችን ይዞ ወደ ዲሎስ ደሴት የሄደው መርከብ እስኪመለስ የሶቅራጥስ ሞት ለአንድ ወር ዘግይቶ ነበር፡፡

 

ስለዚህ ፍርዱ እስኪፈጸም ድረስ በእስር ቤት እንዲቆይ ተደረገ፡፡ ሆኖም የመርከቡ መምጫ ቀን ሲቃረብ ክሪቶን የተባለ የሶቅራጥስ የቅርብ ወዳጅ ከሞት ፍርዱ እንዲያመልጥ ለመነው፡፡ እርሱ ግን በሌሎች ሰዎች የሚወቅሰውን ነገር ከመፈጸም (የህግ የበላይነትን መጣስ) ሞትን መረጠ፡፡

 

ሶቅራጥስ በህዝብ መብት ሥም ይሆን የነበረው ዲሞክራሲያዊ ሁካታ፣ ጋጋታ እና ትርምስ ሁሉ እጅግ ያሳዝነው ነበር፡፡ ሕዝብን ማስተዳደር ልዩ መዘጋጆን ይጠይቃል የሚለው ሽማግሌው ፈላስፋ፤ ህዝብ ልዩ ዝግጅት ያላቸው መሪዎች ሊኖሩት ያስፈልጋል ሲል ይከራከራል፡፡

 

እነዚህ መሪዎች መሠረቱ መልካም ምግባር በሆነ ዕውቀት፣ ሙያ እና ችሎታ የተለዩ እና ከፍተኞች መሆን አለባቸው ሲል አስተምሯል፡፡ የዳኝነት እና የአስተዳደር ሥርዓት አዋቂዎች የሚሆኑ ጥቂቶች እና ዕውቀታቸው ጽድቅ ርትዕን ሠናይ ምግባርን ከለየ ሲመሩ እንጂ የላይ የላዩን ብቻ የሚመለከት ይህን ሁሉ ዘርዝሮ አርቆ ለመገንዘብ የማይችለው ተራ ህዝብ መብት ካገኘሁ ዘንድ የወደድኩት የመሰለኝን ብሎ በሚመርጣቸው ሹማምንት ብዛት የማይከናወኑ የማይጠበቁ መሆናቸው ክርክር ባጋጠመው ቁጥር ሲናገር፤ በፍጥረታዊ መብት ዜጎች የሚያገኙት የእኩልነት መብት፤ በመሪነት እና በአገልግሎት ደረጃ እኩል እንዲሆኑ አያስገድድም በማለት በግልጥ ይናገር ነበር፡፡ በዚህ የተናሳ የሀሳቡ ተቃዋሚዎች የሆኑ በርካቶች ነበሩ፡፡

 

ታዲያ ከፍ ሲል በጠቀስኩት ታሪክ ወይም ሐሳብ ውስጥ ከዴሞክራሲ መርሆዎች ጋር የሚጋጩ ጉዳዮች መኖራቸው እረዳለሁ፡፡ እንዲሁም ዘመን አይሽሬ ነጥቦች መኖራቸውን አውቃለሁ፡፡ እናም ከጠቀስኩት የሶቅራጥስ ታሪክ ውስጥ ሦስት ቁም ነገሮችን በማውጣት ሐሳብ መሰንዘር እፈልጋለሁ፡፡

 

1ኛ) የተጣራም ባይሆን በሰው ህሊና እና አዕምሮ ፍጽምና ያለው እውነት መቻሉና ይህ እውነት ግልጥ ሆኖ እንዲወጣ፤ የሰዎችን ሐሳብ በትምህርት እና በአዕምሮ ምርመራ ማበልጸግ አስፈላጊ መሆኑን፤ ‹‹የዕውቀት መነሻ እና መድረሻ፤ ርትዕ፣ ፍትሕ እና በጎ ምግባር መሆናቸውን፤

 

2ኛ) መሪዎች መሠረቱ መልካም ምግባር የሆነ ዕውቀት፣ ሙያ እና ችሎታ ሊኖራቸው ማስፈለጉን፤

 

3ኛ) ሶቅራጥስ የህግ የበላይነትን ከመጣስ ሞትን መምረጡ ናቸው፡፡

 

ሶቅራጠስ በአስተዳደር ረገድ የነበረው ሐሳብ በግልጽ ወደ ኦሊጋርኪ የሚሳብ ነው፡፡ ሆኖም አስተሳሰቡ ወደ ኦሊጋርኪ የተሳበው፤ ከፍተኛ መንፈስ፣ አዕምሮ እና ክህሎት የታደሉት ሰዎች በሥልጣን ላይ ሁነው አስተዳደር እና ህዝብን አስማምተው ለማካሄድ የሚችሉበትን ሁኔታ ለመፍጠር ያስችላል ከሚል እምነት እንጂ በዘመናችን በአንዳንድ ሐገሮች እንደሚታየው የቶታሊተሪ አስተዳደርን በመፍቀድ አይደለም፡፡

 

እንደሚታወቀው፤ ‹‹ኦሊጋርኪ›› የጥቂቶች አገዛዝ ወይም አስተዳደር ነው፡፡ የሶቅራጥስ ሐሳብ፤ ጥቂቶች ለጥቂቶች ፍላጎት መከበር የሚሰሩበትን አስተዳደራዊ ሁኔታ ማቋቋም አይደለም፡፡ በተቃራኒው፤ ጥቂቶች ለብዙሃኑ ጥቅም የሚሰሩበትን የአስተዳደር ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ ታዲያ ከዚህ ጋር ተያይዞ ሊጠቀስ የሚገባው፤ ‹‹ኦሊጋርኪ በዴሞክራሲ ስርዓት ውስጥ  ሊፈጠር ይችላል›› የሚሉ አንዳንድ ምሁራን መኖራቸው ነው፡፡

 

እነዚህ ምሁራን እንደሚሉት ‹‹በዴሞክራሲ መርህ ላይ ተመስርተው በሥልጣን ክፍፍል የተደራጁ ተቋማት ቀስ በቀስ የፍላጎት (የጥቅም) አንድነት በሚፈጥሩ ፖለቲከኞች (ሥራ ኃላፊዎች) የሚያዙበት ሁኔታ ሲከሰት ኦሊጋርኪ ሊፈጠር ይችላል›› ይላሉ፡፡ ሆኖም ይህ ኦሊጋርኪ ከቀዳሚው የሶቅራጥስ ኦሊጋርኪ የተለየ ነው፡፡ የሶቅራጥስ ኦሊጋርኪ ጥቂቶች ለብዙሃኑ የሚሰሩበትን ሁኔታ ሲያመለክት ሲሆን፤ ኋለኛው ጥቂቶች ለጥቂቶች ጥቅም መከበር የሚሰሩበትን ሁኔታ የሚያመለክት ነው፡፡

 

ዜጎች በፈለጉ ጊዜ የመረጧቸውን ሰዎች ከኃላፊነት ማንሳት በሚችሉበት ሁኔታ የተፈጠረ ‹‹ኦሊጋርኪ›› ከሆነ ይታረማል፡፡ ሆኖም ዜጎች ተጽዕኖ ከማድረግ ያለፈ አቅም በሌላቸው ሁኔታ የተፈጠረ ‹‹ኦሊጋርኪ›› ከሆነ አደገኛ ይሆናል፡፡ ኢህአዴግ ‹‹ቦናፓርቲዝም›› በሚል የገለፀው ይህን ችግር ይመስለኛል፡፡

 

እንደ ኢህአዴግ አመለካከት፤ የስርዓቱ እውነተኛ ባለቤት የሆነው ካፒታሊስቱ (በተለይም የመካከለኛው መደብ) በደንብ ተደራጅቶ ባልወጣበት የፖለቲካ ምህዳር ሥልጣን የያዘው የንዑስ ከበርቴ የመደብ ጀርባ ያለው የአመራር ቡድን፤ አብዮታዊ ባህርይውን ጠብቆ ለመጓዝ የሚቸገርበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡

 

ይህ የንዑስ ከበርቴ መደባዊ ዳራ ያለው የአመራር ቡድን ዴሞክራሲያዊ ባህርይውን በንቃት ጠብቆ ለመጓዝ የሚያስገድደው ማህበራዊ ኃይል ባልተፈጠረበት ሁኔታ፤ አዲስ የገዢ መደብ ሆኖ ሊወጣ ይችላል፡፡ ኢህአዴግ ‹‹ቦናፓርቲዝም›› ሲል የገለጸው ይህን ችግር ነው፡፡

 

ታዲያ እንዲህ ያለ የስርዓት አደጋ መኖሩን የተገነዘበው ኢህአዴግ፤ ድርጅቱን ከዚህ አደጋ በመጠበቅ እና አብዮታዊ ባህርይውን ጠብቆ ለመጓዝ የሚያስችል የጠራ የፖለቲካ መስመር ይዞ ለመውጣት ጥረት ማድረግ ጀመረ፡፡ የሐገሪቱን ተጨባጭ ፖቲካዊ ሁኔታ በዝርዝር በመተንተን ‹‹የህልውና ጉዳይ አድርጎ የሚመለከተውን የዴሞክራሲ ስርዓት ጉዳዮች በመተንተን፤ የዴሞክራሲ ተቋማት ግንባታ ትግሉ በምን መንገድ መመራት እና ከታለመው ግብ ለመድረስ እንዴት መጓዝ እንዳለበት የሚያመለክት ግልጽ የፖለሲ ሰነድ ይዞ መውጣት ቻለ፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ የገጠር ልማት፣ የኢንዱስትሪ ልማት፣ የውጭ ጉዳይ እና የአገራዊ ደህንነት ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎች እና ስልቶችን የሚተነትኑ ሰነዶችን ቀረፀ፡፡ 

 

እነዚህ ሰነዶች አሁን የምንመለከተውን ሁለንተናዊ ለውጥ ለመፍጠር ያስቻሉ በጣም ወሳኝ የለውጥ መሣሪያዎች ናቸው፡፡ ታዲያ ኢህአዴግ እነዚህን ምርጥ የለውጥ መሣሪያዎች መቅረጽ ብቻ አልተወሰነም፡፡ በመሣሪያዎቹ በደንብ ለመጠቀም የሚችል ብቃት እና ክህሎት ያለው ሰው መፍጠር አስፈላጊ መሆኑን ተገንዝቦ የማስፈጸም አቅም ግንባታ ስትራቴጂ እና ፕሮግራም ነድፏል፡፡

 

ገዢው ፓርቲ ያለውን ሐገራዊ የማስፈጸም አቅም ዉሱንነት በመገንዘብ፤ የአቅም ውሱንነት ችግሩን በመፍታት፤ የማስፈጸም አቅምን ለማጠናከር የሚያስችል የአቅም ግንባታ ሰነድ አዘጋጅቶ ተግባራዊ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ታዲያ የማስፈጸም አቅም ግንባታው የአሰራር እና የአደረጃጀት ለውጥ በማምጣት፤ የቁሳቁስ ድርጅትን በማጠናከር ብቻ የሚመዘን አይደለም፡፡ በሰው ኃይሉ የትምህርት ዝግጅት እና የስራ ልምድ የሚገደብ ጉዳይ አይደለም፡፡ ጉዳዩ የአመራር አካሉን የአመለካከት ጥራት የሚመለከትም ነው፡፡ አሁን እየታየ ያለው ችግርም ከዚሁ የመነጨ ነው፡፡  

 

እንደሚታወቀው፤ ከደርግ መደምሰስ ማግስት እስከ 1993 ዓ.ም (ወይም እስከ ኤርትራ ወረራ ድረስ) ባሉት ዓመታት በአጠቃላይ የስርዓቱ መርሆዎች ላይ ያለው የድርጅቱ አመለካከት ግልጽ ቢሆንም፤ የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ዕድገትን ለመፍጠር በሚያስችል ግልጽ የሆነ ፖሊሲ የተመራ ባለመሆኑ በየዘርፉ ያለው ዕድገት አዝጋሚ የነበረበት ሁኔታ ነበር፡፡

በአምባገነን አገዛዝ ሥር በቆዩት የሐገሪቱ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ እና የማህበራዊ ዘርፎች ያሉት ችግሮች መዋቅራዊ ችግሮች ነበሩ፡፡ እናም በቅድመ ተሐድሶው ዘመን ኢህአዴግ ችግሮቹ መዋቅራዊ መሆናቸውን ከመረዳት በቀር ያሉትን ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ግልጽ ፖሊሲ ነድፎ፤ አሰራር እና አደረጃጀቱን አስተካክሎ ለመሄድ የቻለበት ሁኔታ አልነበረም፡፡ እንዲያውም በወቅቱ የነበረው አመራር ሐገሪቱ የገጠማትን ችግር በተለያየ ዓይን የሚመለከት ነበር፡፡ ስርዓቱ አደጋ የተጋረጠበት አደጋ ምንጭ ምንድነው በሚለው ጉዳይ የተለያየ አቋም የሚያራምዱ አመራሮች ነበሩ፡፡ ከዚህ በባሰ አደጋውን ለመለየት የተቸገሩ አመራሮችም ነበሩ፡፡

ስለሆነም የአመራሩ የአመለካከት ልዩነት በድርጅቱ ላይ አደጋን የሚጋብዝ እንቅፋት ሆኖ የቆመበት ወቅት ነበር፡፡ በዚህ ልዩነት ሳቢያም አመራሩ ለሁለት የተከፈለበት ወቅት ነበር፡፡  ትምክህተኝነት፣ ጠባብነት፣ ሙስና እና ፀረ ዴሞክራሲያዊነት የስርዓቱ አደጋ መሆናቸውን በሚቀበል የድርጅቱ አመራር ቡድን እና የስርዓቱ አደጋ ከዚህ የተለየ መሆኑን በሚያምን ሌላ የአመራር ቡድን መካከል የሰላ ትግል ተካሄደ፡፡ ዝርዝሩን ለታሪክ እንተወው፡፡ አሁን ለወቅታዊ ሁኔታችን ተፈላጊ የሚሆነው ነጥብ ድርጅቱ ‹‹የጥገኛ ዝቅጠት›› በሚል የሚጠቅሰው ችግር ነው፡፡ ይህ ችግር አሁን ‹‹ኪራይ ሰብሳቢነት›› በሚል የሚጠቅሰው ነው፡፡ ፖለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ አንድምታ ያለው፤ በአመለካከት እና በተግባር የሚገለጽ ችግር ነው፡፡

 

ኢህአዴግ ይህን ችግር ለማስወገድ የሚያስችል የጥልቅ ተሐድሶ ምዕራፍ ውስጥ ገብቷል፡፡ የዚህ ተሃድሶው ዓላማ በሐገሪቱ የተጀመረውን ለውጥ ማስቀጠል ነው፡፡ ከህዝቡ ፍላጎት ጋር ሲታይ ‹‹አርኪ›› ከሚባል ደረጃ የደረሰ ባይሆንም ተሃድሶው የህዝቡን ጥያቄ እየመለሰ ነው፡፡ የዚህ ጥልቅ ተሐድሶ ዋና ግብም የተጀመረውን ልማት የሚያስቀጥል አቅም መገንባት ነው፡፡

የጥልቅ ተሃድሶው የአንድ ሰሞን ተግባር ሳይሆን ቀጣይነት ያለው ሂደት ነው። በጥልቀት መታደስ ማለት የአስተሳሰብ ለውጥን በማምጣት መልካም አስተዳደርን ማስፈን ነው፡፡ ስለሂነም ‹‹እየታደስን እንሰራለን፤ እየሰራንም እንታደሳለን፡፡››

 

ኢትዮጵያውያን ለሐገር ዕድገት የሚበጁ ጠንካራ ማህበራዊ እሴቶች አሉን፡፡ እነዚህ ማህበራዊ እሴቶች፤ በዴሞክራሲ የፖለቲካ እሴቶች ሲደገፉ ጠንካራ ህብረት ለመፍጠር ያግዙናል፡፡ በሶቅራጥስ ታሪክ ምሳሌ እንደተመለከትነው፤ መሪዎቻችን የህዝባቸውን ሁኔታ በደንብ ለመረዳት መጣጣር፤ ‹‹የዕውቀታቸውም መነሻ እና መድረሻ፤ ርትዕ፣ ፍትሕ እና በጎ ምግባር መሆናቸውን›› ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል፡፡

 

መሪ ድርጅቱም መሪዎቻችን መሠረቱ መልካም ምግባር የሆነ ዕውቀት፣ ሙያ እና ችሎታ ሊኖራቸው ጥረት ማድረግ፤ የጎደለውን ነገር በተከታታይ ግመገማ ማጥራት እና ማስተካከል ይኖርበታል፡፡ እንደ ሶቅራጥስ አባላቱ ‹‹የህግ የበላይነትን ከመጣስ ሞትን የሚመርጡ›› ሆነው እንዲገነቡ ጥረቱን ማጠናከር ይገባዋል፡፡

 

የዴሞክራሲ እሴትን እና ‹‹የጋራ ህሊና›› (collective awareness) ማህቶትን በግማሽ ልብ የመያዝ ችግር እንዲወገድ መሥራት ይኖርበታል፡፡ ለምሁራዊ እና ጥበባዊ ወይም ቁሳዊ ዕድገት የሚመች ሁኔታ እንዲዳብር የሚያደርግ ሁኔታ በመፍጠር፤ በተከታታይ እና በረጅም ዘመን የባህል እና የታሪክ ድር የተሸመነው የኢትዮጵያዊነት መንፈስ እንዳይሻሽር አድርጎ፤ እንደ ሐገር ያለን ህልውና እንዲቀጥል የረዳንን የፌዴራላዊ ስርዓት መርሆዎች ማጠናከር ይኖርብናል፡፡