የላሙ ወደብ የመርከብ ማቆያ ተመረቀ

ግንቦት 13/2013 (ዋልታ) – የኢትዮጵያ፣ የኬንያ እና ደቡብ ሱዳን የጋራ ፕሮጀክት አካል የሆነው የላሙ ወደብ የመጀመሪያው የመርከብ ማቆያ በኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ሙይጋይ ኬንያታ ዛሬ ተመርቋል።

ፕሬዚዳንት ኬንያታ የላሙ ወደብ ስራ መጀመሩን አብስረው የመጀመሪያዋ መርከብም በወደቡ መልህቋን ጥላ ዕቃ አራግፋለች።

ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ የላሙ ወደብ ግንባታ መከናወን ሶስቱን የምስራቅ አፍሪካ ሃገራት በንግድ እና የአገልግሎት ዘርፍ በማስተሳሰር ብዙ የስራ ዕድል እንደሚፈጥር ጠቅሰው÷ ሌሎችም የፕሮጀክቱ አካላት ስራዎች እንዲፋጠኑ አሳስበዋል።

በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ የተገኙት በኬንያ የኢትዮጵያ አምባሳደር መለስ ዓለም ኢትዮጵያ ለላሙ ፕሮጀክቶች መሳካት አስፈላጊውን አስተዋፅኦ ታደርጋለች ብለዋል።

ከናይሮቢ-ሞያሌ-አዲስ አበባ መንገድ መመረቅና የሞያሌ የአንድ መሰኮት ኬላ አገልግሎት መጀመር ጋር ተደምሮ የወደቡ መከፈት የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን እንደሚያጠናክረው መናገራቸውን ኬንያ ከሚገኘው የኢትዮጵያ ኤምባሲ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።