የኢትዮጵያ መንግስት የወሰደው ተኩስ አቁም ጥሩ እርምጃ መሆኑን አሜሪካ አስታወቀች

ሰኔ 23/2013 (ዋልታ) – የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ ክልል የወሰደው የተኩስ አቁም እርምጃ መልካም እርምጃ መሆኑን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

የተኩስ አቁም ሂደቱ ግጭትን ካስቆመ፣ እንዲሁም የሰብአዊ ድጋፎች ያለ ገደብ ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች እንዲደርስ ለማድረግ ካስቻለ ውጤታማ እንደሚሆን ነው የተገለጸው፡፡

የኢትዮጵያን ሉዓላዊነት እና የግዛት አንድነት ለመጠበቅ እንዲሁም በትግራይ መረጋጋት እንዲመጣ ሁሉም  አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያደርጉ አሜሪካ ጠይቃለች፡፡

ሁሉም ወገኖች ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ህግን በጥብቅ እንዲያከብሩ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች እና በደሎች ተጠያቂነት እንዲኖሩባቸው  መደረግ እንደሚገባ በመግለጫው ተጠቅሷል፡፡

አሜሪካ በትግራይ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ድጋፍ ለማድረግ ከሌሎች ዓለም አቀፍ አጋሮች ጋር በትብበር ለመስራት ዝግጁነት እንዳላት ተገልጿል፡፡