የጥምቀት በዓልን የሚያከብሩ ምዕመናን የአፍና አፍንጫ ጭምብል ማድረግ አለባቸው – የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት

የጥምቀት በዓልን ለማክበር ወደ ጥምቀት ባህር የሚሄዱ ምዕመናን የአፍና አፍንጫ ጭምብል ማድረግ ግዴታ እንደሆነ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ መምህር አካለወልድ ተሰማ ገለጹ፡፡
የእምነቱ ተከታዮች ወደ አደባባይ ሲወጡ ያልተፈቀዱ ተግባራትን ከመተግበር እንዲቆጠቡም አሳስበዋል፡፡
በዓሉ ሀይማኖታዊ ስርዓትን በጠበቀ መልኩ ሊከበር እንደሚገባ ያሳሰቡት ዋና ስራ አስኪያጁ፣ ምዕመናን ለአምልኮ ወደ ጥምቀተ ባህር ሲያቀኑ የአፍና አፍንጫ መሸፈኛ ጭምብል የማድረግ ግዴታ እንዲወጡም አስታውቀዋል፡፡
በዓሉ በሰላም እና ፀጥታ እንዲያልፍ ምዕመናን የበኩላቸውን ኃላፊነት እንዲወጡም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
(በሀኒ አበበ)