የእንጦጦ ፓርክ የመኪና ማቆሚያ የግንባታ ሥራ ተጠናቀቀ

ጥር 17/2014 (ዋልታ) የእንጦጦ ፓርክ የመኪና ማቆሚያ የግንባታ ፕሮጀክት ሙሉ በሙሉ ተጠናቆ ለአገልግሎት ክፍት መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን አስታወቀ፡፡
ይህ ፕሮጀክት በአጠቃላይ ሦስት የመኪና ማቆሚያ ግንባታዎችን የያዘ ሲሆን ሁለቱ በእንጦጦ ፓርክ ዋና መግቢያ በር እንዲሁም ሦስተኛው በሱሉልታ መግቢያ በኩል የተገነቡ ናቸው፡፡
እነዚህ የመኪና ማቆሚያዎች 14 ሺሕ 63 ካሬ ሜትር ስፋት ያላቸው ሲሆን በአንድ ጊዜ 450 መኪና ማቆም የሚያስችሉ ናቸው፡፡
የመኪና ማቆሚያ ሥፍራዎቹ በተለይም እንጦጦ ፓርክን ለመጎብኘት ለሚመጡ የከተማዋ ነዋሪዎች እና የውጭ ቱሪስቶች ቆይታቸውን ምቹ እንደሚያደርግላቸው ከአዲስ አበባ ከተማ መንገዶች ባለሥልጣን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡