ሁለቱ ተቋማት በጋራ ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረሙ

ግንቦት 11/2014 (ዋልታ) የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን እና የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት በጋራ መስራት የሚያስችላቸውን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርመዋል።

የስምምነት ፊርማውን የሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ስመኝ ውቤ እና የኢትዮጵያ ጥራት፣ ሽልማት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈጻሚ ቴዎድሮስ መብራቱ ተፈራርመውታል።

የሲቪል ሰርቪስ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ጥራት በገለልተኛ አካል ሊመዘን እንደሚገባ የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ስመኝ ውቤ ገልጸዋል።

የሲቪል ሰርቪስ መስሪያ ቤቶችም ግዴታቸውን መወጣታቸው የሚረጋገጠው የአገልግሎት አሰጣጣቸው ጥራት በገለልተኛ አካል ተመዝኖ ሲረጋገጥ እንደሆነ አስገንዝበዋል።

ኮሚሽኑ መንግሥታዊ አገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል የሚያስችሉ የተለያዩ ሥራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ የጠቆሙት ምክትል ኮሚሽነሯ ጥራት ያለው፣ ተደራሽና ፈጣን መንግሥታዊ አገልግሎት ለዜጎች መስጠት የሲቪል ሰርቪሱ ግዴታ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡

የኢትዮጵያ ጥራት ሽልማት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈፃሚ ቴዎድሮስ መብራቱ በበኩላቸው የፌዴራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ተቋማት ዓለም ዐቀፍ መስፈርትን በጠበቀ መልኩ ገለልተኛ በሆነ ተቋም መመዘን ይገባቸዋል ብለዋል።

ከዚህ ባለፈም ደረጃ እንዲወጣላቸው ማድረጉ ሀገራዊ ኃላፊነት ካለበት ከአንድ ተቋም የሚጠበቅ ነው ማለታቸውን የኢዜአ ዘገባ አመላክቷል፡፡

ለፈጣን መረጃዎች፦
ፌስቡክ https://bit.ly/3Ma7QTW