በሲዳማ ክልል ለጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይና መንግስታቸው የድጋፍ ሰልፍ እየተካሄደ ነው

የሲዳማ ክልል ነዋሪዎች ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር ዐቢይ አህመድና የሚመሩትን መንግስት በመደገፍ በሀዋሳ ህዝባዊ ሰልፍ እያካሄዱ ነው።

የድጋፍ ሰልፉ የለውጡን ሂደት የመምራት ሀላፊነት ወስደው ወደስልጣን ከመጡ ወዲህ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድና መንግስታቸው ላሳዩት አመርቂ ውጤት የምስጋናና የዕውቅና ለመስጠት ያለመ መሆኑም ተገልጿል።

ከክልሉ ከሁሉም ወረዳዎችና ከተሞች የተውጣጡ በሺህዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች ዛሬ ከጧቱ 12:00 ጀምሮ ህዝባዊ ሰልፍ በመውጣት የድጋፍ ድምጻቸውን እያሰሙ ነው።

ነዋሪዎቹ የሲዳማ ክልል ከለውጡ መሪ ከዶክተር ዐቢይ አህመድ ጎን ነው፤ ክልላችን የለውጡ ውጤት ነው የሚሉ መፈክሮችን በማንገብና በማሰማት ድጋፋቸውን በመግለጽ ላይ ናቸው።

ሰልፈኞቹ በአሁን ሰአት የድጋፍ ድምጻቸውን በጋራ ወደ ሚያሰሙበት ሀዋሳ ዓለም አቀፍ ስታዲየም በማምራት ላይ ይገኛሉ ሲል ኢዜአ ዘግቧል።