በአዲስ አበባ ዘመናዊ የስታርትአፕ ከተማ መገንባት የሚያስችል ስምምነት ተፈረመ

ጳጉሜን 1/2015 (አዲስ ዋልታ) የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴርና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ዘመናዊ የስታርትአፕ ከተማ ለመገንባት የሚያስችል ስምምነት ሰነድ ፈርመዋል፡፡

ስምምነቱን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) እና የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች አበቤ ናቸው የተፈራረሙት፡፡

የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር በለጠ ሞላ (ዶ/ር) በዚሁ ወቅት እንደገለፁት አስተዳደሩ ያለውን አቅም በመጠቀም ሐብት ሊፈጥሩ የሚችሉ ሐሳቦችን ወደ ስታርትአፕ በመቀየር አምራች ኩባንያዎች የሚፈጠሩበትና ማህበረሰቡ ተጠቃሚ የሚሆንበትን ስርዓት ለመፍጠር እንሰራለን ብለዋል፡፡

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አዳነች በበኩላቸው መተባበር ከቻልን ብዙ መስራት የሚያስችለን አቅም አለን ማለታቸውን የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር መረጃ ያመላክታል፡፡

በቴክኖሎጂው ዘርፍ ላይ ከሚኒስቴሩ ጋር በትብብር በመስራት በርካታ ዜጎችን የሀብት ባለቤት ለማድረግ በትኩረት እንሰራለን ብለዋል፡፡

ከዩኒቨርሲቲዎች የተመረቁ ተማሪዎችን በቴክኖሎጂው ዘርፍ እንዲሰማሩ ጥቂት እገዛ በማድረግ እውቀታቸውን ተጠቅመው በቀላሉ ሀብት እንዲያፈሩ መሰራት እንዳለበትም ተጠቁማል፡፡

ዘመናዊ የስታርትአፕ ከተማን በመገንባት÷ የስራ ቦታን፣ የስልጠና ማዕከላት፣ አይ ሲ ቲ ፓርክ፣ የተሰጥኦ ትምህርት ቤት እና ሌሎች ምቹ አካባቢዎችን ለማሟላት የትብብር ስራው ተጠናክሮ እንዲቀጥል ተስማምተዋል፡፡