ቦርዱ የትግራይ ክልልን ጨምሮ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ባልተካሄደባቸው አካባቢዎች እና አካባቢያዊ ምርጫን በ2016 ዓ.ም ለማካሄድ ማቀዱን ገለጸ

ግንቦት 2/2015 (ዋልታ) የትግራይ ክልልን ጨምሮ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ባልተካሄደባቸው አካባቢዎች እና አካባቢያዊ ምርጫን በ2016 ዓ.ም ለማካሄድ ማቀዱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ገለጸ።

ቦርዱ የ2015 በጀት ዓመት ያለፉት 9 ወራት የዕቅድ አፈጻጸም ግምገማ ሪፖርት ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አቅርቧል።

ሪፖርቱን ያቀረቡት የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢ ውብሸት አየለ በተለያዩ ችግሮች ምክንያት በተወሰኑ ክልሎች በሚገኙ አካባቢዎች 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ አለመካሄዱን ገልጸዋል። ይህንኑ ምርጫ ለማካሄድ በ2015 ዝግጅት ለማድረግ ታቅዶ እንደነበርም ተናግረዋል።

በሌላ በኩል የአካባቢ ምርጫ ለማካሄድ ቢታቀድም አለመሳካቱን ገልጸው እነዚህን ምርጫዎች በ2016 ለማካሄድ ቦርዱ ዕቅዱን ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማቅረቡን ተናግረዋል።

ባለፉት ወራት ከፖለቲካ ፓርቲዎች አሠራር ጋር በተያያዘ አንዳንድ ፓርቲዎች ጠቅላላ ጉባኤ እንዳያካሂዱ በተለያዩ አካላት መከልከላቸውን ቦርዱ ማረጋገጡን እና አንዳንድ የፓርቲ አመራሮች ለእስር መዳረጋቸውን ገልጸዋል።

ቦርዱ ለዚህ ችግር መፍትሔ ለመስጠት ሥራዎችን እየሠራ መሆኑን የቦርዱ ምክትል ሰብሳቢው መናገራቸውን ኢቢሲ ዘግቧል።