ትናንት ሌሊት በደረሰ የእሣት አደጋ 1.5 ሚሊዮን ብር በሚገመት ንብረት ላይ ጉዳት ደረሰ

መጋቢት 30/ 2013 (ዋልታ) – “በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለከተማ በደረሰ የእሣት አደጋ 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ንብረት ጉዳት ደርሶበታል” ሲል የከተማዋ እሣትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር ባለስልጣን ገለፀ።

የባለስልጣኑ የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ ጉልላት ጌታነህ ለኢዜአ እንደገለጹት፤ በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 2 መካኒሳ አካባቢ ትናንት ሌሊት 10 ሠዓት አካባቢ ለጊዜው መንስኤው ያልታወቀ የእሣት አደጋ ተከስቷል።
“በአደጋው 1 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር የሚገመት ንብረት ላይ ጉዳት የደረሰ ሲሆን 7 ሚሊዮን ብር ግምት ያለው ንብረት ማትረፍ ተችሏል” ብለዋል።
ባለስልጣኑ መረጃው እንደደረሰው 35 የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች፣ ስድስት ከባድ የአደጋ ተሽከርካሪዎችና አንድ አምቡላንስን በማሰማራት እሣቱን በ30 ደቂቃ ውስጥ መቆጣጠር መቻሉን ገልጸዋል።
በ45 ካሬ ላይ የደረሰው የእሣት አደጋ በመኖሪያ ቤቶችና በንግድ ሱቆች ላይ መሆኑን አቶ ጉልላት አክለዋል።
የአደጋውን መንስኤ ለማጣራት በፖሊስ ምርመራ እየተደረገ ሲሆን ውጤቱ በተለይም አደጋው ለደረሰባቸው አካላት ይፋ የሚደረግ እንደሆነም ነው ያስረዱት።
በእሣቱ በሰው ላይ የአካል ጉዳትም ሆነ የሞት አደጋ አለመከሰቱን ጠቅሰው፤ አደጋውን ለመቆጣጠር ርብርብ ላደረጉ የፖሊስ አባላትና ለአካባቢው ኀብረተሰብ ምስጋና አቅርበዋል።