አምባሳደር ሽፈራው ገነቲ ከባህሬን የአሰሪና ሰራተኞች ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈጻሚ ጋር ተወያዩ

ግንቦት 12/2015 (ዋልታ) በባህሬን የኢትዮጵያ ቆንስል ጀነራል አምባሳደር ሽፈራው ገነቲ ከባህሬን የአሰሪና ሰራተኞች ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈጻሚ ኖፍ አብዱልራህማን ጃምሺር ጋር ተወያይተዋል።

ሁለቱ ወገኖች በባህሬን በሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ጥበቃ ላይ ፍሬያማ ውይይት ማድረጋቸውን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል።

አምባሳደር ሽፈራው የባህሬን የአሰሪና ሰራተኞች ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ለኢትዮጵያዊያን ዜጎች እየሰጣቸው ለሚገኙ አገልግሎቶችና ድጋፍ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውርን መዋጋትና የኢትዮጵያ ሰራተኞች በወቅቱ ክፍያቸውን የሚያገኙበትን ሁኔታ ማረጋገጥ ላይ በትብብር መስራት እንደሚያስፈልግ አመልክተዋል።

የባህሬን የአሰሪና ሰራተኞች ተቆጣጣሪ ባለስልጣን ዋና ስራ አስፈጻሚ ኖፍ አብዱልራህማን ጃምሺር በበኩላቸው ለጉልበት ብዝበዛና ሕገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር የተዳረጉ ሰራተኞች በመጠለያ በማቆየት የሚያስፈልጋቸው ድጋፍ እንደሚደረግላቸው ገልጸዋል።