አቶ ደመቀ መኮንን ከኮሞሮስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ተወያዩ

May be an image of 1 person, standing, sitting and indoor
ሚያዚያ 26 /2013 (ዋልታ) ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከኮሞሮስ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከዱዋሂር ዱልካማል ጋር በሁለትዮሽ ግንኙነት እና ታለቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን አስመልክተው ውይይት አደረጉ፡፡
ዱዋሂረ “የሰው ዘር መገኛ አገር በመምጣት ደስተኛ ነኝ “ በማለት የኮሞሮስ ህዝብና መንግሰት ሰላምታ አቅርበዋል፡፡
በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው የረጅም ጊዜ ታሪካዊ ግንኙነት በመዳሰስ፤ በኢንዱስትሪ ፣ በባህል ፣በስልጠ እንዲሁም በህክምና ዘርፍ በተለይም የኮሮና በሽታን በጋራ ለመከላከል በጋራ ለመሥራት ጥሪ አቅርበዋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ለኮሞሮስ ዜጎች ተመራጭ መሆኑንና ግንባር ቀደም አገልግሎት ሰጭ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ከህዳሴ ግድብ ጋር በተያያዘ በግብፅና ሱዳን ጉብኝት በማድረግ ከሚመለከታቸው ባለሥልጣናት ጋር መነጋገራቸውን ጠቅሰው፤ በአገሮቹ መካከል ያለው ልዩነት በሰላም እንዲጠናቀቅ የፕሬዝዳንታቸውን መልዕክት አቅርበዋል፡፡
በግድቡ ላይ የሚስተዋሉ አለመግባባቶች በሰላማዊ መንገድ እንዲፈታ ፤ አገራቸው የበኩሏን ድርሻ ለመጫወት ፍላጎት ያላት መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አቶ ደመቀ በበኩላቸው በሁለቱ አገሮች መካከል ያለው ታሪካዊ ግንኙነት በማስታወስ ፤ ግንኙነቱ የበለጠ ማጠናከር አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበዋል፡፡
በኮሞሮስ በኩል ትብብር እንዲደረግባቸው ለቀረቡ መስኮች በጥናት ታይተው የሚመለሱ መሆኑን አመላክተዋል፡፡
የአፍሪካ ህብረት የመሪዎች ጉባኤ ቢሮ አባል በመሆናቸው ፤ ከግድቡ ጋር ተያይዞ ላቀረቡት ሃሳብ አቶ ደመቀ አድናቆታቸው ፡፡
አያይዘውም ኢትዮጵያ የአባይን ውሃ 86 በመቶ አመንጭ መሆኗን ጠቅሰው፤ ግብጽ ግን ከወንዙ ለረጅም ጊዜ በብቸኝነት ስትጠቀም የቆየች አገር መሆኗን አስረድተዋል፡፡
ምክንያታዊ፣ ፍትሃዊ ተጠቃሚነት እና ለታችኞቹ አገሮች ጉልህ ጉዳት አለማድረስ በሚል መርህ የህዳሴ ግድብ እየገነባች መሆኑን ገልጸው ፤ በአሁኑ ጊዜ ግድቡ 80 በመቶ አፈጻጸሚ ላይ እንደሚገኝ አቶ ደመቀ አብራርተዋል፡፡
የግድቡ ግንባታም ሆነ ውሃ ሙሌቱ እ.ኤ.አ. በ2015 በተፈረመው የመርሆች መገለጫ ስምምነት (DOP) መሰረት እየተካሄደ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
ሱዳን ከዚህ በፊት ግድቡ እንደሚጠቅማት ስትገልጽ ቢትቆይም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ሀሳቧን በመለዋወጥ በአፍሪካ ህብረት እየተካሄደ የሚገኘውን የሶስትዮሽ ድርድር እያደናቀፈች መሆኑን ለሚኒስትሩ አስረድተዋል ፡፡
ለአፍሪካ ችግር አፍሪካ መፍትሔ ከሚለው መርህ በተቃራኒ የግድቡን ጉዳይ ፖለቲካዊና ዓለም አቀፋዊ መልክ እንዲኖረው እየተደረገ መሆኑን አቶ ደመቀ አስገንዝበዋል::
የአፍሪካ ህብረት ቢሮ ጉዳዩ በሰላም እንዲያልቅ እያደረገ ያለን ጥረት እንደሚያደንቁ ገልጸው ፤ በበርካታ መድረኮች ላይ ኮሞሮስ ከኢትዮጵያ ጎን በመቆም አጋርነት በማሳየትዋ ምስጋና አቅርበዋል፡፡
ውይይቱ በሁለቱም ወገኖች በኩል መግባባት የተፈጠረበት ውጤታማ እንደነበር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስታውቋል ፡፡