አየር መንገዱ ላይ እየተሰሙ ያሉ ቅሬታዎችን መርምሮ መፍትሄ ለመስጠት እየሰራሁ ነው – የኢትዮጵያ አየር መንገድ


መጋቢት 3/2016 (አዲስ ዋልታ) የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰሞኑን እየተሰሙ ያሉ ቅሬታዎችን መርምሮ መፍትሄ ለመስጠት እየሰራ መሆኑን ገለፀ፡፡

በዚህም አየር መንገዱ በአዲስ አበባ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ አገልግሎት ከሚሰጡ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ቅሬታዎችን የማጣራት ስራ እየሠራ መሆኑን አሳውቋል፡፡

አየር መንገዱ ከሰሞኑ በተለያዩ የማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ የሚቀርቡበትን ቅሬታዎች አስመልክቶ ያስተላለፈው መልዕክት እንደሚከተለው ይቀርባል….

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሰሞኑን በቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ከመንገደኞች አገልግሎት አሠጣጥ ጋር በተያያዘ በተለያዩ የማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ ቅሬታዎች እየተነሱ መሆኑን ተገንዝቧል።

አየር መንገዱ ከክቡራን ደንበኞቹ ለሚቀርቡ ቅሬታዎች እና አስተያየቶች ከፍተኛ ትኩረት የሚሠጥ በመሆኑ ሂደቱን በጥሞና ሲከታተል ቆይቷል።

በመሆኑም እየተሰሙ ያሉ ቅሬታዎችን መርምሮ መፍትሄ ለመስጠት አየር መንገዱ በአዲስ አበባ ቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ውስጥ አገልግሎት ከሚሰጡ ሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ቅሬታዎችን የማጣራት ስራ እየሠራ መሆኑን ለማሣወቅ እንወዳለን።

ይህንንም ተከትሎ በማጣራቱ ሥራ ላይ በሚገኙ ውጤቶች ላይ በመመርኮዝ ተገቢው የማስተካከያ እርምጃ በፍጥነት እንዲወሠድ ይደረጋል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሁልጊዜም ጥረቱ ለውድ ደንበኞቹ ቀልጣፋ እና ምቹ አገልግሎት መስጠት ነው። አሁንም የክቡራን ደንበኞቹን ጥቆማ ተቀብሎ አስፈላጊውን ማስተካከያ በማድረግ ይህንኑ ጥረቱን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በአክብሮት እንገልጻለን።