ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች ዝርዝር ላይ ማሻሻያ ተደረገ

ኅዳር 9/2015 (ዋልታ) ላልተወሰነ ጊዜ የውጭ ምንዛሬ የማይፈቀድላቸው ከውጭ የሚገቡ ዕቃዎች ዝርዝር ላይ ማሻሻያ መደረጉን የገንዘብ ሚኒስቴር ገለጸ፡፡

ከዚህ ቀደም ላልተወሰነ ጊዜ ተላልፎ በነበረው የውጭ ምንዛሬ የማይፈቀድላቸው ከውጭ የሚገቡ እቃዎች ዝርዝር ላይ ማሻሻያ ማድረግ በማስፈለጉ ከዚህ በታች በተዘረዘሩት ዕቃዎች ላይ ማሻሻያ መደረጉን የገንዘብ ሚኒስቴር ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ባንክና ለጉምሩክ ኮሚሽን በጻፈው ደብዳቤ አስታውቋል፡፡

በዚህም መሰረት ማሻሻያ የተደረገባቸው ከውጭ የሚገቡ እቃዎች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

1. በታሪፍ ቁጥር 9401.9000 እና 9403. 9000 የሚመደቡ እቃዎች ክፍሎች ማምረቻ ግብአቶች፣

2. ምርቶቻቸውንና አገልግሎቶቻቸውን በውጭ ምንዛሬ የመሸጥ ፍቃድ ያላቸው ሬስቶራንቶችና ሱፐር ማርኬቶች የራሳቸውን የውጭ ምንዛሬ ተጠቅመው የሚያስገቧቸው ዕቃዎች፣

3. ባለ ኮከብ ሆቴሎች የራሳቸውን የውጭ ምንዛሬ ተጠቅመው የሚያስመጧቸው ዕቃዎችና
4. የቀረጥ ነጻ ሱቆች የሚያስመጧቸው ዕቃዎች የውጭ ምንዛሬ ክልከላው የማይመለከታቸው መሆኑን ከገንዘብ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡

ላልተወሰነ ጊዜ የውጭ ምንዛሬ የማይፈቀድላቸው ከውጭ የሚገቡ የ38 እቃዎች ዝርዝር በጥቅምት ወር 2015 ዓ.ም ይፋ መደረጉ የሚታወስ ነው፡፡

ለፈጣን መረጃዎች፦
ፌስቡክ https://bit.ly/3Ma7QTW