የበግና ፍየል ሳንባ በሽታ መከላከያ ክትባት ማምረቻ መሳሪያ ሥራ ጀመረ

ኢትዮጵያ የበግና ፍየል ሳንባ በሽታ በቴክኖሎጂ የመከላከል አቅምን የሚያሳድግ የክትባት መሙያ እና የሌብሊንግ ማሽን ቢሾፍቱ ከተማ በሚገኘው ብሔራዊ የእንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት ግቢ ስራ አስጀመረች።

በአፍሪካ ከፍተኛ ጉዳት በማድረስ ከሚታወቁ የእንስሳት በሽታዎች መካከል የበግና ፍየል ሳንባ በሽታ(PPR) ተጠቃሽ ነው።

ይህን በሽታ ከአርብቶ አደር አካባቢዎች ለማስወገድ የግብርና ሚንስቴር እና ብሔራዊ የእንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት ከተባበሩት መንግስታት የምግብ እና እርሻ ድርጅት እንዲሁም ከአውሮፓ ህብረት ጋር ላለፉት 7 አመታት ያህል በቅንጅት ሰርቷል።

በሽታው ተላላፊ ከመሆኑም ባሻገር በተከሰተበት አካባቢ 70 በመቶ የመግደል አቅም ያለው ሲሆን በኢትዮጵያም ጉዳት ሲያደርስ እንደነበር ተጠቁሟል።

ይሁንእንጂ ብሔራዊ እንስሳት ጤና ጥበቃ ኢንስቲትዩት በሽታው የሚያስከትለውን ኢኮኖሚያዊ ጉዳት ለመቀነስ የበሽታውን መከላከያ ክትባት ሲያመርት ቆይቷል።

ክትባቱን አርሶ አደሮች እና አርብቶ አደሮች በሚገኙባቸው የሀገሪቱ አካባቢዎች ከማሰራጨት አልፎ ለበርካታ የአፍሪካ ሀገራት ማዳረስ ተችሏል ተብሏል።

የአውሮፓ ህብረት ለክትባት መሙያ እና ሌብሊንግ ማሽኑ ግዢ ወደ 900 ሺህ ዩሮ የሚጠጋ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉም ተጠቅሷል።

(በደረሰ አማረ)