ዩኒቨርሲቲው ከ4 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የምግብና ቁሳቁስ ድጋፍ አደረገ

የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ከ4 ሚሊየን ብር በላይ ግምት ያላቸው ምግብና ቁሳቁስ ለመተከል ተፈናቃዮች እና በሕግ ማስከበሩ ሂደት ጉዳት ለደረሰባቸው የክልሉ የጸጥታ ኃይሎች ድጋፍ አድርጓል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ምርምርና ማህበረሰብ አገልግሎት ምክትል ፕሬዚደንት ዶክተር ተስፋየ ሽፈራው እንደገለጹት ዩኒቨርሲቲው በመተከል ለተፈናቀሉ ዜጎች እና በሕግ ማስከበሩ ሂደት ጉዳት ለደረሰባቸው የክልሉ ጸጥታ ኃይሎች የምግብና የቁሳቁስ ድጋፍ አድርጓል፡፡

ዩኒቨርስቲው 660 ኩንታል በቆሎ፣ 3 ሺህ 300 ሊትር ዘይት፣ ፓስታ፣ ሩዝ፣ ብርድ ልብስ፣ ፋራሽ፣ አንሶላና የንጽህና መጠበቂያ ሳሙና ድጋፍ ያደረገ ሲሆን ይህም ከ4 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሚገመት ዶክተር ተስፋየ ገልጸዋል፡፡

የአማራ ክልል አደጋ መከላከል፣ ምግብ ዋስትና እና ልዩ ድጋፍ የሚሹ አካባቢዎች ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር ወይዘሮ እታገኘሁ አደመ እንደገለጹት በዩኒቨርሲቲው የተደረገው ድጋፍ ከሌሎች ድጋፎች ጋር በማቀናጅት በመተከል ለተፈናቀሉ ዜጎች እና በሕግ ማስከበር ሂደቱ ወቅት ችግር ለደረሰባቸው የልዩ ኃይል እና ሚሊሻ አባላት የችግሩን ስፋት በመለየት ተደራሽ ይሆናል፡፡

የባሕርዳር ዩኒቨርሲቲ ከዚህ በፊትም ድጋፎችን ሲያደርግ እንደነበር የገለጹት ምክትል ኮሚሽነሯ ሌሎች የሕብረተሰብ ክፍሎች እና ተቋማትም ተፈናቃዮች ሰላም ተረጋግጦ ወደ ቀያቸው እስኪመለሱ ድረስ ድጋፋቸውን በተደራጀ መንገድ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል፡፡

(ምንጭ፡- አብመድ)