ጀርመን ለኢትዮጵያ የ80 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዩሮ ድጋፍ ልታደርግ ነው

የካቲት 14/2014 (ዋልታ) ጀርመን ለኢትዮጵያ የ80 ነጥብ 6 ሚሊዮን ዩሮ ድጋፍ ለማድረግ ቃል መግባቷ ተገለፀ።

ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ከጀርመን የኢኮኖሚ ትብብር እና ልማት ሚኒስትር፣ ከስዊድን እና አየርላንድ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሮች ጋር ተወያይተዋል፡፡

በውይይቱ በሁለቱ አገራት መካከል ባለው የሁለትዮሽ ግንኙነት እና በኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ላይ መምከራቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ አመላክቷል፡፡

በተመሳሳይ ሚኒስትሩ ከስዊድን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ከአየርላንድ የውጭ ጉዳይና መከላከያ ሚኒስትር ጋር በሁለትዮሽ እና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡

በዚህም የኢትዮጵያን ሁኔታ በተመለከተ በሰጡት ማብራሪያ መንግሥት ለሰላም ፅኑ አቋም እንዳለው ጠቅሰው በሰሜን ኢትዮጵያ ያለው ጦርነት ሰላማዊ መፍትሄ እንዲያገኝ የተለያዩ ጠንካራ ውሳኔዎችን ማሳለፉን ተናግረዋል።

ሆኖም አሸባሪው ትሕነግ ጠብ አጫሪነቱን በመቀጠል አጎራባች ክልሎች ላይ ጥቃት እየፈፀመ መሆኑን አብራርተዋል።

የአገራቱ ሚኒስትሮች በበኩላቸው የኢትዮጵያ መንግሥት እየወሰዳቸው ያሉ ሰላምን ለማምጣት የሚያገዙ እርምጃዎች የሚደነቁ ናቸው ብለዋል።