ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ መስተዳድር የሚሆን የአንድነት ንቅናቄን አስጀምሩ

 

ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ

የካቲት 11/2013 (ዋልታ) – ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ የክልል ፕሬዚዳንቶች እና የከተማ ርዕሰ መስተዳድሮች ለትግራይ ክልል ጊዜያዊ መስተዳድር እንዲሁም ለክልሉ ሕዝብ የሚሆን የአንድነት ንቅናቄን አስጀምረዋል።

ንቅናቄው ዛሬ ከሰዓት በበይነ መረብ በታገዘ ስብሰባ መጀመሩን ነው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ያስታወቀው፡፡

የአንድነት ንቅናቄው ክልሎች፣ የፌደራል ተቋማት እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻ አካላት በመከናወን ላይ ያለውን ሰብዓዊ እርዳታ እንዲደግፉ የማስቻል ዓላማን መያዙ ተነግሯል።

በጊዜያዊ አስተዳደሩ አማካኝነት ለትግራይ ሕዝብ ከሚደርሱ ምግብ እና ምግብ ነክ ያልሆኑ አቅርቦቶች በተጨማሪ፣ የክልል ፕሬዚዳንቶች አስተዳደሩ የሕዝብ አገልግሎት አሰጣጥ ግዴታዎቹን ለመወጣት እንዲችል ቀጥተኛ ድጋፍ ለማድረግ ቃል ገብተዋል።

በዚህም መሠረት፣ እያንዳንዱ ክልል ቃል የገባቸው ተሽከርካሪዎች፣ ልዩ ልዩ ቁሳቁስ እና መገልገያዎች፣ ለአርሶ አደሮች የሚቀርቡ ዘሮች፣ አምቡላንሶች፣ መድሃኒት እንዲሁም የገንዘብ ድጋፍ በሚቀጥሉት ቀናት ለጊዜያዊ አስተዳደሩ እንደሚደርሱ ነው የተገለጸው።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ሁሉም የኢትዮጵያ ሕዝብ ትግራይን መልሶ ለመገንባት የአንድነት ንቅናቄው የሚችለውን አስተዋጽኦ ሁሉ እንዲያደርግ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።