ቢሮው የአንበሳ አውቶቢስን ለማዘመን እየሠራ ነው

የአዲስ አበባ የመንገድ ትራንስፖርት ቢሮ  የአንበሳ አውቶቢስ አገልግሎትን በ20 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር  ለማዘመን  የተለያዩ ሥራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ  አስታወቀ ።

ከዓለም ባንክ   በተገኘ  የ20 ሚሊዮን  ዶላር  ድጋፍ  የአንበሳ አውቶቢስን የትራንስፖርት እንቅስቃሴና አስተዳደራዊ ሥራዎችን በማዘመን   የአዲስ አበባ ከተማ  ውጤታማ የሆነ የመንገድ ደህንነትን ለመፍጠር ጥረት እየተደረገ ይገኛል ።

የቢሮው  ምክትል ሃላፊ  አቶ  ምትኩ አስማረ ለዋልታ እንደገለጹት የአንበሳ አውቶቢስን ለማዘመን የሚካሄደው ፕሮጀክት በየጊዜው  በአዲስ  አበባ ከተማ  እያደገ የመጣውን የትራንስፖርት  አገልግሎት ፍላጎት  ለማስተናገድ ያግዛል  ብለዋል ።

የአንበሳ አውቶቢስን የመዘመን  ሥራው  ሲጠናቀቅ  በኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎች  ቲኬት  መቁረጥ እንደሚቻልና የጂፒሴስ ቴክኖሎጂም እንደሚገጠም የገለጹት  አቶ ምትኩ  ፕሮጀክቱ ባለፈው ዓመት የተጀመረ  ሲሆን  በሚቀጥሉት  ሁለት ዓመታት  የማዘመን ሥራው ይጠናቀቃል ተብሎ ይገመታል ብለዋል ።

የአንበሳ  አውቶብስ  አገልግሎት የላላና በዘመናዊ መልኩ  ያልተደራጀ  ቁጥጥር  በመኖሩ ምክንያት አንድ አውቶቢስ በቀን 21  ዙር  ደንበኞችን  ማመላለስ  ሲገባው  13  ዙር ብቻ  የሚያመላልስ መሆኑን አቶ ምትኩ አስረድተዋል ።

ቢሮው   የከተማዋን  የትራንስፖርት  ችግር  ለመቅረፍ   በአማራጭነት  የሸገር አውቶቢስ፣ የአሊያንስ አውቶቢስና የአዲስ አበባ ቀላል  ባቡር  የትራንስፖርት አገልግሎቶች  እንዲጀመሩ  ማድረጉን  አቶ ምትኩ ገልጸዋል ። 

በአዲስ  አበባ  ፈርቀዳጅ  የትራንስፖርት  አገልግሎት  ሰጪ የሆነው የአንበሳ ትራንስፖርት  አገልግሎት ድርጅት ለ70 ዓመት  ያህል  ለህብረተሰቡ  አገልግሎት የሠጠ ሲሆን  በአሁኑ ወቅት  500  አውቶቢሶችን በማሠማራት  በ124  መሥመሮች  አገልግሎት  እየሠጠ ነው ።

የአዲስ አበባ  ከተማ  በየጊዜው   እያደገች  ከመምጣቷም  ባሻገር  የህዝብ ቁጥሯም እየጨመረ  በመምጣቱ   የከተማ ነዋሪው የትራንስፖርት  አገልግሎት ፍላጎትም  በፍጥነት  እያደገ  መምጣቱ የተለያዩ መረጃዎች ይጠቁማሉ ።

የአዲስ  አበባ  ከተማ   ከሰሃራ በታች ከሚገኙ  10 ትላልቅ ከተሞች  አንዷ ስትሆን እ.ኤ.አ በ 2020 የከተማ ህዝብ ቁጥር አሁን ካለበት 4 ሚሊዮን  8  ሚሊዮን ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል  ዘግቧል ።

ትርጉም ሰለሞን ተስፋዬ