ኤጀንሲው 15 ቢሊዮን ብር የሚያወጡ መድሓኒቶችና የህክምና መሣሪያዎች ግዥ እንደሚፈጽም አስታወቀ

በአዲሱ በጀት ዓመት 15 ቢሊዮን ብር  የሚያወጡ መድሓኒቶችና  የህክምና መገልገያ መሣሪያዎችን  ግዥ ለማከናወን  አቅዶ  እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ የመድሓኒት ፈንድና  አቅርቦት  አጄንሲ አስታወቀ ። 

የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ሎኮ አብርሃም ለዋልታ እንደገለጹት፤  15 ቢሊዮን  ብር የሚያወጡ 1ሺ 400 አይነት መድሓኒቶችንና የህክምና መገልገያ መሣሪያዎችን  ግዥ በማከናወን ለተጠቃሚዎች ለማሠራጨት  ታቅዶ እየተሠራ ይገኛል ።

ባለፈው የበጀት ዓመት ኤጀንሲው 13 ቢሊዮን ብር የሚያወጡ መድሓኒቶችንና የህክምና መሣሪያዎችን ለህብረተሰቡ አገልግሎት እንዲውሉ ማድረጉን የጠቆሙት ዶክተር ሎኮ  መድሓኒቶቹ ከአገር ውስጥና  ከውጭ  የተገዙ ናቸው  ብለዋል ።

ኤጄንሲው በአገሪቱ እጅግ ተፈላጊ የሆኑ 420 የሚሆኑ የተለያዩ የህክምና መገልገያ መሣሪያዎችን በመለየት የህክምና ተቋማት በቀጥታ ያለንም ውጣ ውረድ የሚገዙበትን የአሠራር ሁኔታን  መዘርጋቱን ዶክተር ሎኮ አስረድተዋል ።

በተለይ ትልልቅ ካፒታል  የሚጠይቁትን  የህክምና  የመገልገያ መሣሪያዎችን   በዓመት  ሦስት   ጊዜ   በጨረታ  እንዲገዙ  በማድረግ  በመላ አገሪቱ የሚገኙ  ተቋማት  በአግባቡ  እንዲስተናገዱ ጥረቶች  እየተካሄዱ መሆኑን  ዶክተር ሎኮ ገልጸዋል ።

እንደ ዶክተር ሎኮ ገለጻ  ኤጀንሲው ዓምና  የነበረው  63 በመቶ  የመድሓኒት  አቅርቦትን በ2010  95  በመቶ   ለማድረስም  ዕቅድ ወጥቶ  ተግባራዊ  ለማድረግ ከወዲሁ  እንቅስቃሴዎች  ጀምረዋል ።  

እስካሁን ድረስ  በአገር ውስጥ  የሚገኙት  የመድሓኒት  አምራቾች  10 በመቶ  ብቻ  የሚሆነውን   የመድሓኒት  አቅርቦት  ብቻ  እየሸፈኑ  እንደሚገኙ ጠቁመው፤በአገሪቱ የመድሓኒት  አምራቾች እንዲበራከቱ በርካታ የማበረታቻ  ሥርዓትን  መዘርጋቱን አብራርተዋል ።

የመጠቀሚያ  ጊዜያቸው  ከ 80 በመቶ በላይ  የሆኑ  መድሓኒቶች  የጥራት  ደረጃቸው ተረጋግጦ ወደ አገር ውስጥ እንደሚገቡ  አመልክተዋል፡፡

የመድሓኒቶችን የጥራት ደረጃ ይበልጥ ለማረጋጋጥ ኤጄንሲው ከሌሎች አገር አካላት በተጨማሪ የራሱን የጥራት ማረጋገጫ  ላብራቶሪ  በማደራጀት ላይ መሆኑን አስታውቀዋል ።

የመድሓኒት ፈንድና  አቅርቦት  አጄንሲ  የመጠቀሚያ ጊዜ  ያለፈባቸውን መድሓኒቶችና የህክምና መገልገያ  መሣሪያዎችን  የሚያስወግድበት ሥፍራ የሌለው በመሆኑ  ለረጅም ጊዜ  ሲቸገር የቆየ ሲሆን  በመጪው ዓመታት 8 የማስወገጃ ማዕከላትን ለማስገንባት ዕቅድ ማውጣታቸውን ጠቁመዋል  ።