የ2010 አዲስ ዓመት አቀባበል አካል የሆነው የሀገር ፍቅር ቀን ዛሬ በተለያዩ መርሃ ግብሮች በመከበር ላይ ይገኛል።
የሀገር ፍቅር ቀን “እጃችን እስኪሻክር እንሰራለን ምክንያቱም ኢትዮጵያን እንወዳታለን” በሚል መሪ ቃል ነው በመላው ሀገሪቱ በመከበር ላይ የሚገኘው።
በዛሬው እለትም በተለያዩ ስፍራዎች ከጠዋቱ 4፡00 ሰዓት እስከ 4 ሰዓት 05 ድረስ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ህዝብ መዝሙር በመዘመርና ሰንደቅ ዓላማ በመስቀል የሀገር ፍቅር ቀን ተከብሯል።
በዓሉ ከተከበረባቸው ስፍራዎች ውስጥም የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አንዱ ሲሆን፥ በበዓሉ ላይ የምክር ቤቱ ምክትል አፈጉባዔ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለን ጨምሮ የፌደራል ፖሊስ አባላት እና ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተወጣጡ ሰዎች ተገኝተዋል።
በበዓሉ ላይ ምክትል አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ ሰንደቅ ዓላማ የሰቀሉ ሲሆን፥ በበዓሉ ላይ የታደሙ ሰዎችም ከፌደራል ፖሊስ ማርሽ ባንድ ጋር በመሆን የሀገሪቱን ብሄራዊ መዝሙር በጋራ ዘምረዋል።
ምክትል አፈ ጉባዔ ወይዘሮ ሽታዬ ምናለ በዚሁ ጊዜ ባስተላለፉት መልእክትም፥ ሀገሪቱ በአሁኑ ሰዓት የትራንስፎርሜሽን እቅድ ትግበራ ላይ ትገኛለች፤ ከዚሁ እኩል ፈጣን የኢኮኖሚ እድገት እያስመዘገበች መሆኑን ተናግረዋል።
ወይዘሮ ሽታዬ አክለውም፥ “ቀደም ባሉት ጊዜያት ጀግኖች አባቶች ለኢትዮጵያ ህይወታቸውን ሰውተዋል ደማቸውንም አፍሰዋል፤ አሁን ግን ሀገሪቱ ሰላማዊ ናት” ብለዋል።
ከአዲሱ ትውልድ የሚጠበቀውም የሀገር ፍቀር ስሜትን በማጎልበት የሀገሪቱ ዋነኛ ጠላት የሆነውን ድህነትን ድል መንሳት ነው ሲሉም ምክትል አፈ ጉባዔዋ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።