ባለሥልጣኑ 100 ጥንታዊ የብራና መጻሃፍትን ለብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻሓፍት ኤጀንሲ አስረከበ

የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን በህገወጥ መንገድ ሲዘዋወሩ የነበሩ 100 ጥንታዊ የብራና መጻህፍትን ለብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻህፍት ኤጀንሲ አስረከበ

ጥንታዊ ቅርሶቹ በህገወጥ መንገድ በሀገር ውስጥ ሲዘዋወሩ እና ከሀገር ሊወጡ ሲሉ በህብረተሰቡና በፖሊስ ትብብር ተይዘው የማጣራት ሂደት ተደርጎባቸው በፍርድ ቤት ውሳኔ አግኝተው መስከረም 30 ፣2010 ዓ.ም ለቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን የተመለሱ ናቸው፡፡

የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ ዮናስ ደስታ በርክክቡ ወቅት እደተናገሩት ለቅርሶቹ የተሻለ እንክብካቤ ለማድረግ እና ለጥናትና ምርምር እንዲውል በማሰብ ነው ማስረከብ የተፈለገው ብለዋል፡፡

የብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መጻህፍት ኤጀንሲ ዋና ዳሬክተር አቶ ይኩኖአምላክ መዝገቡ የብራና መጽሐፍቱን በማይክሮ ፊልም በማስቀረፅ ዲጂታላይዝ በማድረግ ለትውልድ እንዲተላለፍ ይደረጋል ብለዋል፡፡

ከእድሜ ብዛት የተጎዱ መጻህፍት ተገቢው ጥገናና እንክብካቤ ይደረግላቸው ያሉት አቶ ይኩኖአምላክ ፤በውስጣቸው ያለውን የተከማቸ ሀብት ለማጥናት ለሚፈልጉ ተመራማሪዎች አገልግሎት እንደሚሰጡም ተናግረዋል፡፡

ከጥንታዊ መጻህፍት መካከል የብሉይ እና የሀዲስ ኪዳን መጻህፍት፣ድርሳናት፣ድጓ፣ ጾመድጓ፣ የቅዱስ ያሬድ ዜማዎች፣ የጸሎት መጻህፍትና የጥበብ መጻህፍት ይገኙበታል ተብሏል፡፡