በአገሪቱ ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት ጥያቄ ውስጥ ከገቡ መንግሥት እርምጃ ይወስዳል -ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዐቢይ

ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላምን ፣ ዴሞክራሲና ልማትን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ሁኔታ ሲፈጠር መንግሥት አስፈላጊውን እርምጃ  እንደሚወስድ ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዐቢይ ።

ጠቅላይ ሚንስትር ዶ/ር ዐቢይ በዛሬው ዕለት ወቅታዊ ጉዳዮችን በተመለከተ ከምክር ቤት አባላት ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች በሠጡት  ማብራሪያ እንደገለጹት  መንግሥት   በአሁኑ ወቅት የፖለቲካ ምህዳሩ  ለማስፋት የተለያዩ ጥረቶችን ሲያደርግ መቆየቱን ተናግረዋል ።

መንግሥት የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት የወሰነው በአገሪቱ ሰላም፣ ዴሞክራሲና ልማት  የለምንም እንቅፋት  እንዲረጋገጥ መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚንስትሩ  የፖለቲካው ምህዳርን ይበልጥ እንዲሰፋ  ለማድረግ ግን የሁሉም አካላት  ትብብር አስፈላጊ ነው ብለዋል ።

ህዝብን አስተባብሮና አንድ አድርጎ  መታገል  የተለየ የፖለቲካ  አመራር ጥበብን የሚጠይቅ መሆኑን የገለጹት ጠቅላይ  ሚንስትሩ የትኛውም የፖለቲካ ኃይል የአገሪቱ ሰላምን ፣ ዴሞክራሲንና ልማትን ጥያቄ  ውስጥ በሚያስገባ መልኩ ልታገል ካለ ግን መንግሥት አስፈላጊውን  እርምጃ  ይወስዳል ብለዋል ።

የኢትዮጵያን አንድነት  የሚገዳደር  ጉዳይ ላይ የሚሠራ  ኃይል በኢትዮጵያ ላይ  ጦርነት እንዳወጀ  የሚቆጠር በመሆኑ  ሁሉም የፖለቲካ ቡድኖች ፣ ግለሰቦችና ፓርቲዎች አገሪቱን አደጋ ላይ ከሚጥል ተግባር ሊቆጠቡ እንደሚገባ አስገንዝበዋል ።

መንግሥት የማይተች አካል አይደለም ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ የተቃውሞ ድምጽን ማሰማትና  አገራዊ አንድነትን  መገዳደር  የተለያዩ  ተግባራት መሆናቸውን  ተናግረዋል ።

 መንግሥት ከ 20 በላይ  የታጠቁና ያልታጠቁ  የፖለቲካ ኃይሎች ወደ አገሪቱ እንዲገቡ  የፈቀደው  የአገሪቱን ሁለንተናዊ  ለውጥ  ይበልጥ  ለማፋጠን   በማሰብ  መሆኑንና ይህም  ለህዝብ ተወካዮች  ምክር  ቤት ትልቅ ድል መሆኑን ለምክር ቤቱ ገልጸዋል ።

የትኛውም አካል ለመንግሥት የሚያቀርባቸውን ጥያቄዎች እንዲመለሱ ለማድረግ  የሓሳብ ትግል በማድረግ  ብቻ  የሚፈጸምና በአገሪቱ የሚንቀሳቀሱ ሁሉም  የፖለቲካ አካላት ብቃት ስላለኝ  ታግዬ  አሽንፋለው የሚል  አስተሳሰብን መፍጠር  ይኖርባቸዋል ብለዋል ጠቅላይ ሚንስትሩ ።     

ኢትዮጵያ ውስጥ  ምርጥ የሪፎርም ሥራ  ከሠሩ ተቋማት ውስጥ  የመከላከያ ኃይል አንዱ ነው ያሉት ጠቅላይ ሚንስትሩ መከላከያ በብሔር ተዋጽኦን በመጠበቅ ፣ በአገሪቱ የተከሰቱ ግጭቶችን በማብረድ  በኩል  መልካም ሥራን በማከናወኑ ሊወቀስ አይገባም ብለዋል ።

በተለያዩ የአገሪቱ ዩኒቨርስቲዎች የሚማሩ ተማሪዎች የፖለቲካ ነጋዴዎች መጠቀሚያ እንዳይሆኑ  የሓሳብ  ፍጭት  እንጂ  በድንጋይ  ውርወራ  ላይ መሠማራት የተማረ  ሰው መገለጫ ባህሪ አለመሆኑን አስረድተዋል ።

በአገሪቱ እየታየ ያለውን ህገ-ወጥ የመሣሪያና የገንዘብ ዝውውርን በተመለከተ ኢህአዴግ በተሃድሶው ያየው ጉዳይ መሆኑን የጠቆሙት ጠቅላይ ሚንስትሩ ህገ ወጥ የጦር መሣሪያዎች  እንዲገቡ በማድረግ  ችግር  ለመፍጠር የሚፈልጉ አካላት እንዳሉ ገልጸዋል ።

በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ ሉዓላዊ አገር እንጂ  ሉዓላዊ ክልል የለም ስለዚህም ሁሉም  ዜጋ  በፈለገው ክልል ና ቦታ  ተዘዋውሮ መሥራትና ህይወቱን  መምራት  የሚችልበት ሁኔታም  መፈጠር  እንዳለበት ጠቅላይ ሚንስትሩ አጽዕኖት ሠጥተው ተናግረዋል ።

በአገሪቱ  የሚፈጠሩ ግጭቶችን  ለማስቆምና ዘላቂ ሰላም  ለማስፈን  የሰላም ሚኒስቴር  ተቋቁሞ የአገር ሽማግሌዎች ፣ የሃይማኖት አባቶችና ምሁራን  በጋራ እየሠሩ ስለመሆኑ  ጠቅላይ ሚንስትሩ ለምክር ቤቱ አባላት  አብራርተዋል ።

በመጨረሻም  በወንጀል  ተጠርጥረው  ለፍርድ እየቀረቡ ያሉ ግለሰቦች  ሰብዓዊ መብቶቻቸው ተጠብቆ ጉዳያቸው እየታየ መሆኑንና ማንኛውም ዜጋ ወንጀል ፈጽሞ የትም መደበቅ እንደማይችልና  ቢደበቅ እንኳን ህሊናው ነጻ እንደማይሆን ተናግረዋል ።