ኢህአዴግ በፖለቲካ ጉዳዮችና ቀጣይ እርምጃዎች በመወያየት አቅጣጫዎችን አስቀመጠ

የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በፖለቲካ ጉዳዮችና ቀጣይ እርምጃዎች በመወያየት አቅጣጫዎችን አስቀመጠ

የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ትናንት ሰኔ 10 ቀን 2011 ዓም ባካሄደው ስብሰባ በሀገራችን ወቅታዊ የፖለቲካ ሁኔታ ላይ በመወያየት በቀጣይ ስለሚወሰዱ እርምጃዎች አቅጣጫዎች ማስቀመጡን የኢህአዴግ ም/ቤት ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

ኮሚቴው የአንድ ዓመት የፖለቲካ ስራዎች፤ ወቅታዊ ሀገራዊ የፖለቲካ ሁኔታዎችና በቀጣይ ትኩረት ስለሚሹ ጉዳዮች ውይይት አድርጓል፡፡ ባለፈው አንድ ዓመት በፖለቲካው መስክ በርካታ ስኬቶች የተመዘገቡ ቢሆንም፤ በአገሪቱ የጸጥታ መደፍረስ፣ በአመራር ቁርጠኝነት ማነስ፣ የጋዜጠኝነት፣ አክቲቪስትነትና ፖለቲከኝነት መምታታት እየተስተዋሉ መሆናቸውን ገምግሟል፡፡ ኮሚቴው የአመራር ቁርጠኝነት ማነስ እየተከሰቱ ያሉ ችግሮች በአጭር እንዳይቀጩና መልካቸውን እየቀያየሩ እንዲከሰቱ እያደረጉ በመሆኑ ይህንን በፍጥነት ማስተካከል እንደሚገባም አስምሮበታል፡፡ በየደረጃው ያለው አመራር በየዘርፉ እየተከሰቱ ያሉትን ችግሮች ለመቅረፍ መርህንና ህግን አክብሮ መስራት እንደሚገባ አቅጣጫ አስቀምጧል፡፡

የእነዚህ ችግሮች ዋናው መንስዔ የሀገሪቱ የፖለቲካ ጥያቄዎች የወለዳቸው ተያያዥነት ያላቸው ታላላቅ ሀገራዊ ተግዳሮቶች በአንድ ጊዜ በሀገራችን መደቀናቸው መሆኑን የተመለከተው ኮሚቴው፤ እነዚህም ገለልተኛ እና ብቃት ያላቸው መንግታዊ ተቋማት አለመገንባት፤ በወሳኝ ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ ስምምነት እሴት መጓደል እንዲሁም ውጤታማ መንግስታዊ አስተዳደር አለመጠናከር መሆናቸው አይቷል፡፡የሀገረ -መንግስት፤ የብሔር መንግስትና፣ የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ መሰረታዊ ጥያቄዎች አፍጥጠው የመጡና አፋጣኝ መፍትሔ የሚፈልጉ መሆናቸውንም በዝርዝር ገምግሟል፡፡ 
ተግደሮቶቹ በመድብለ ፓርቲ ስርዓት ግንባታ ላይም ችግሮችን እያስከተሉ መሆናቸው የገመገመው የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ጠንካራ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች እና ሲቪል ማህበራት ለዴሞክራሲው ስርዓት ግንባታ ካላቸው አስተዋጽኦ አንጻር እያደረጉት ያሉትን አንቅስቃሴ ተመልክቷል፡፡ ተፎካካሪ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከለውጡ ጋር ተያይዞ በነጻነት የሚንቀሳቁበት ሁኔታ ቢፈጠርም ተቋማዊ አቅም ካለመኖርና ከፖለቲካ ድርጅቶቹ ብዛትና የአጀንዳ ግልጽነት ችግር ጋር ተያይዞ መድበለ ፓርቲ ስርዓቱን ለማጠናከር ተጨማሪ ስራዎች እንደሚቀሩ አስምሮበታል፡፡

ከሀገራችን ነበራዊ ሁኔታ አንጻር ጠንካራ ሲቪክ ማህበራት ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታው ወሳኝ በመሆናቸው ከዚህ መስክ ተጨማሪ ስራ እንደሚጠበቅ አስምሮበታል፡፡ 
የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ኢህአዴግ እንደ አንድ ተፎካካሪና ገዥ ፓርቲ የመድብለ ፓርቲ ስርዓትን ለማጠናከር መወሰድ ስለሚገባቸው እርምጃዎችና ቀጣዩን ምርጫ በሚመለከት ጉዳይ ላይም መክሯል፡፡

ሀገራችን እያደረገችው ያለችው ሁለንተናዊ ለውጥ መዳረሻው የዴሞክራሲያዊ ስርዓትና ገለልተኛ ተቋማት በመገንባት አንድነቷ የተጠበቀ ዴሞክራሲያዊት ሀገር ለመገንባት ያለመ በመሆኑ የተሳካና ተአማኒነት ያለው ምርጫ ማድረግ ልንደርስበት ላለምነው ጉዞ ወሳኝ ድርሻ እንደሚወጣ አጽንኦት በመስጠት ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታና ለተሳካ ምርጫ መስራት የግድ እንደሚል አመልክቷል፡፡

የመድብለ ፓርቲ ስርዓን የሚያጠናክሩ ዝንባሌዎችን በማጎልበት፣ ለፖለቲካ ተሳተፎ ምቹ የሆነ በሕግና በስርዓት ብቻ የሚመራ የፖለቲካ ምህዳር በመፍጠር፤ ፓርቲዎች የፖለቲካ ዓላማቸውን ለማሳካት ከሌሎች ጋር በትብብር እንዲሰሩ በማረታታት የሚከናወን እንደሆነ አጽንኦት ሰጥቶ ማየቱን የኢህአዴግ ም/ቤት ጽ/ቤት አስታውቋል፡፡

EPRDF official