ኢትዮጵያ የጎረቤት አገር ስደተኞች በማስተናገድ እያበረከተች ያለውን አስተዋጽኦ ተመድ አደነቀ

የተባበሩት  መንግሥታት  ድርጅት የስደተኞች  ከፍተኛ ኮሚሽነር ሚስተር ፍሊፖ ግራንዲ  ኢትዮጵያ   የጎረቤት አገር ስደተኞችን ተቀብላ በማስተናገድ ረገድ  እያበረከተች   ያለውን   አስተዋጽኦ  አደነቁ ።        

ኮሚሽነሩ  በዛሬው ዕለት 17ኛው  የዓለም አቀፍ  የስደተኞች ቀንን በማስመልከት በጉኑል  የስደተኞች መጠሊያ  ካምፕ ባደረጉት  ጉብኝት  እንደገለጹት “ ኢትዮጵያ  ለስደተኞች በሯን ክፍት በማድረግ ምሳሌ የምትሆን አገር ናት ”  ።  

እንደ ኮሚሽነሩ ገለጻ ኢትዮጵያ የጎረቤት አገር ስደተኞችን  ከማስተናገድ በተጨማሪ  ሥልጠናና ትምህርት እንዲያገኙ በማስቻል  ስደተኞች  የወደፊት ህልማቸውን እውን  እንዲያደርጉ እገዛ  እያደረገች ነው ።

ኮሚሽነሩ   በዛሬው ዕለት  የዓለም  የስደተኞች ቀንን  በማስመልከት ባደረጉት  ንግግር  መላው  የዓለም አቀፍ የሰብዓዊ ድጋፍ ድርጅቶች  ለስደተኞችን  ለአስፈላጊው  እርዳታ   ምላሽ  እንዲሠጡ ጥሪ  አቅርበዋል ።  

የዓለም አቀፉ ማህበረሰብ  በደቡብ ሱዳን ያጋጠመውን  ፖለቲካዊና ሰብዓዊ  ቀውስ መፍትሄ እንዲያገኝም መሥራት እንደሚገባው መልዕክት  አስተላልፈዋል ።     

የኢፌዴሪ  የውጭ  ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ወርቅነህ  ገበየሁ በበኩላቸው  ኢትዮጵያ  የተለያዩ  ችግሮች ቢኖሩም  ለጎረቤት አገራት   ስደተኞች በሯን  ክፍት ማድረጓን  ይገልጿል ።  

የዓለም አቀፍ ማህበረሰብ  ከኢትዮጵያ ተሞክሮ  ልምድ በመውሰድ  በመላው ዓለም የሚገኙ ስደተኞችን  ለመደገፍ  እጅ ለእጅ  በመያያዝ   የስደተኞችን   አሰቃቂ ህይወት   መታደግ ይገባዋል  ብለዋል ።

ኢትዮጵያ   በምስራቅ አፍሪካ  እያሳደረች ያላው ዲፕሎማሲያዊ  ተጽዕኖ እያደገ በመምጣቱ  17ኛውን የዓለም  የስደተኞችን  ቀን  እንድታዘጋጅ   ያስቻላት መሆኑን ተናግረዋል ።

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ   850 ሺህ  የሚሆኑ  የሱዳን ፣ የደቡብ ሱዳን ፣ የሶማሊያና  የኤርትራ  ስደተኞችን በማስተናገድ ላይ ትገኛለች ።

በመላው ዓለም  65 ሚሊየን   ህዝብ  በተለያዩ  አገራት  በስደት የሚገኝ ሲሆን  1 በመቶ የሚሆኑ  ብቻ  ወደ ትውልድ አገራቸውና መንደራቸው  ይመለሳሉ  ።