ሚንስቴሩ በበጀት ዓመቱ 48ሺህ ቤተሰቦችን በመንደር ለማሰባሰብ ማቀዱን አስታወቀ

ዘንድሮ በስድስት የአርብቶ አደር ክልሎች ከ48ሺህ በላይ ቤተሰቦችን በመንደር በማሰባሰብ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ተጠቃሚ ለማድረግ  መታቀዱን  የፌደራል ጉዳዮችና  አርብቶ አደር አካባቢ ልማት ሚኒስቴር አስታወቀ ።

በሚኒስቴሩ የህዝብ ግንኙነትና ኮሚኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ አበበ ወርቁ ለዋልታ እንደገለጹት በተያዘው የበጀት ዓመት በአፋር ፣ በሶማሌ፣ በኦሮሚያ ፣ ደቡብ ፣ ቤኒሻንጉልና ጋምቤላ  ክልሎች  አርብቶ አደር አካባቢዎች የሚገኙ 48ሺህ39  ቤተሰቦችን  በአዳዲስ የመንደር ማሰባሰቢያ ማዕከላት በማሰባሰብ የተለያዩ መሠረታዊ አገልግሎቶች ተጠቃሚ ለማድረግ እንቅስቃሴ  እየተካሄደ ይገኛል ።

ሚኒስቴሩ  ባወጣው ዕቅድ መሠረት በሶማሌ ክልል 15ሺህ ፣ በአፋር 15ሺህ ፣ በኦሮሚያ 4ሺህ ፣ በደቡብ 9ሺህ 410 ፣ በጋምቤላ  3ሺህ 886 እና በቤኒሻንጉል ጉምዝ  743 የሚሆኑ  ቤተሰቦችን  ወደ አዳዲስ  መንደሮች  ለማስገባት እየተሠራ መሆኑን አቶ አበበ ጠቁመዋል    

በስድስቱም ክልሎች ተግባራዊ በሚደረገው የመንደር ማሰባሰብ ፕሮግራም በአጠቃላይ 441  የሚደርሱ የተለያዩ  መሠረታዊ  የኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ተገንብተው   ለአርብቶ አደሩ  አገልግሎት መሥጠት  እንደሚጀምሩ አቶ  አበበ አመልክተዋል ።

በክልሎቹ የሚካሄደው የመንደር ማሰባሰብ  ፕሮግራም  ስኬታማ እንዲሆን  ለማድረግ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ  ከወዲሁ ከፌደራል ፣ ከክልል ፣ ከዞን ፣ ወረዳ ፣ የቀበሌ አመራሮችና  ከአርብቶ አደሩ  ጋር ግንዛቤ የመፍጠርና የማግባባት ሥራዎች እንደሚካሄዱ አቶ አበበ አስገንዝበዋል ።

የፌደራል ጉዳዮችና አርብቶ አደር አካባቢ ልማት ሚኒስቴር  በነደፈው የመንደር ማሰባሰብ ፕሮግራም በአጠቃላይ 365ሺህ 909 የሚደርሱ የአርብቶ አደር ቤተሰቦችን በመንደር ማዕከላት በማሰባሰብ ሙሉ ለሙሉ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ አገልግሎቶች ተጠቃሚ የማድረግ ዕቅድ አለው