ዩኒቨርስቲው 3ሺህ 105 ተማሪዎችን ለመቀበል መዘጋጀቱን አሰታወቀ

የወላይታ-ሶዶ  ዩኒቨርስቲ  በዘንድሮ የትምህርት ዘመን  3ሺህ 105  አዳዲስ  ተማሪዎችን ለመቀበል  ከወዲሁ  ዝግጅቶችን ማጠናቀቁን  አስታወቀ ።

የወላይታ- ሶዶ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚደንት ዶክተር ሰንበቴ ቶማ  ለዋሚኮ እንደገለጹት በ2010 የትምህርት ዘመን ዩኒቨርስቲው 3ሺህ 105 የሚሆኑ  አዳዲስ  ተማሪዎችን በመቀበል  በ50 የትምህርት ዘርፎች  ለማስተማር  ተዘጋጅቷል ።

እንደ ዶክተር ሰንበቴ ገለጻ ዩኒቨርሰቲው አዳዲስ ተማሪዎችን ጥቅምት 6 እና 7 2010 ዓም  በሦስቱ  ካምፓሶች  ለማስገባት  አስፈላጊ  መሰናዶዎችን   በሙሉ አጠናቋል ።

የወላይታ -ሶዶ ዩኒቨርስቲ   የተማሪዎች ቅበላ  አቅሙን  ለማሳደግ  ትምህርት  ሚኒስቴር በመደበለት  የ470 ሚሊዮን  ብር በጀት  የመማሪያ ክፍሎች ፣ የመሠረተ ልማትና የቢሮዎች ግንባታን  እያከናወነ ይገኛል  ።

ዩኒቨርሰቲው  የማስፋፈያ ግንባታዎች ሙሉ ለሙሉ  በማጠናቀቀም   በአጠቃላይ   ተማሪዎች የማስተናገድ አቅሙን  17ሺህ  ለማድረግ  ዕቅድ መያዙን  ዶክተር ሰንበቴ  አመልክተዋል ።

የወላይታ -ሶዶ ዩኒቨርስቲ በ2009 የትምህርት  ዘመን 2ሺህ  የሚሆኑ ተማሪዎችን በ50 የትምህርት   ዘርፎች ማስመረቁ  ይታወሳል ።