ሚኒስቴሩ የመማር ሂደቱን የሚያውኩ ተማሪዎች በህግ ተጠያቂ እንደሚያደርግ አስታወቀ

በጥቂት ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ የመማር ማስተማር ሂደቱ እንዲስተጓጎል የሚያደርጉ ተማሪዎችን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ እንደሚሰራ ትምህርት ሚኒስቴር አስታወቀ።

ሚኒስትሩ ዶክተር ጥላዬ ጌቴ ዛሬ በከፍትኛ ትምህርት ተቋማት ላይ የሚታዩትን ወቅታ ሁኔታዎች አስመልክተው በሰጡት መግለጫ በተወሰኑ ዩኒቨርሲቲዎችም ጥቂት ተማሪዎች ትምህርት እንዲስተጓጎል እያደረጉ መሆኑ የተደረሰበት መሆኑን አስታውቀዋል።

እነዚህን ተማሪዎች በህግ ተጠያቂ የማድረግ ስራ እንደሚሰራ የገለጹት ዶክተር ጥላዬ ፤ ተጠያቂ የማድረጉ ሃላፊነትም የሁሉም ዜጋ ነው ብለዋል።

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ መምህራን እና ወላጆች ተቋማቱ ወደ መረጋጋት እንዲመለሱ ርብርብ እንዲያደርጉ ነው ጥሪ የቀረበው።

ወላጆች ልጆቻቸው ያሉበትን ሰላማዊ ሁኔታ ክትትል እንዲያደርጉ ጠይቀዋል ፡፡

ሚኒስትሩ ተማሪዎችም ያላቸውን ጥያቄ ህጋዊ አካሄድን ተከትለው ማቅረብ እንደሚገባቸው መክረዋል።

ተቋማቱም የተማሪዎችን ጥያቄ በአግባቡ ሊመልሱና ከአቅም በላይ የሆኑትን ለትምህርት ሚኒስቴር በማሳውቅ ምላሽ እንዲያገኙ ማድረግ ይገባቸዋል ነው ያሉት።

ከዚህ ውጭ ሰላምን ማደፍረስ የሚፈልጉ ጥቂት ተማሪዎችን ተጠያቂ ለማድረግ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማህበረሰብ የማጋለጥ ስራ እንደሚሰራ ነው ያመለከቱት ።

አሁን ላይ በመቱ፣ አምቦና የመሳሰሉ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ የተጠየቁት ሚኒስትሩ፤ በተቋማቱ የሚማሩ ተማሪዎች ወደ መጡበት እንዲመለሱ እየተደረገ ነው የሚሉ አስተያየቶች ትክክለኛ እንዳልሆኑ አረጋግጠዋል።

ከተማሪዎች እና ከሚመለከታቸው አመራሮች ጋር በመሆን ችግሮችን ለመፍታት ውይይት እየተደረገ መሆኑን ነው የገለፁት።

የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚመሩት በፌደራል መንግስት ቢሆንም ክልላዊ የመሆን አዝማሚያ እየታየባቸው ነው የሚል ጥያቄ ለዶክተር ጥላዬ ቀርቦላቸዋል።

ሚኒስትሩ በምላሻቸው የክልል መንግስታት ተቋማቱን የማረጋጋት፣ ሰላም እንዲሰፍን የማድረግ እና ተቋማቱ የምርምር ማዕከል እንዲሆኑ የማገዝ ስራን ይሰራሉ ብለዋል።

ሆኖም ክልልቹ በተቋማቱ ላይ እየወሰኑ ነው የሚል አስተሳሰብ ሊኖር እንደማይገባ ነው ያስገነዘቡት።

የመወሰን እና የማስተዳደር ስልጣን ያለው እና እየሰራ የሚገኘውም በአሁኑ ሰዓት የፌደራል መንግስቱ ነው ብለዋል።

የኦሮሚያ እና የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልሎች ተማሪዎች ከዚህ ቀደም በክልላቸው እና በሌሎች ክልሎች በሚገኙ  እንዲመደቡ መደረጉን ጠቅሰዋል።

ይህ የተደረገው ክልሎቹ ላይ በተፈጠረው ወቅታዊ ሁኔታ ምክንያት ተማሪዎቹ አካባቢው እስኪረጋጋ ድረስ በየክልላቸው እና በሌሎች ክልሎች በሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች እንዲመደቡ በትምህርት ሚኒስቴር በመወሰኑ ነው ያነሱት ሚኒስትሩ።

ነገር ግን ይህ እንደማይቀጥል እና የክልሎቹ ሰላማዊ ሁኔታ ሲመለስ፤ ቀድሞ ወደተመደቡበት የከፍተኛ ትምህርት ተቋም እንዲመለሱ እንደሚደረግ ዶክተር ጥላዬ ጌቴ አስታውቀዋል።

ህብረ ብሔራዊነት በሚገለፅባቸው የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሰላምን ለማደፍረስ በሚጥሩ ጥቂት ተማሪዎች የመማር ማስተማር ሂደቱ መስተጓጎል እንደሌለበት ሚኒስትሩ አስገንዝበዋል።

በሃገራችን  36 የመንግስት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ከ700 ሺህ በላይ ተማሪዎች፥ እየተማሩ ሲሆን፤ ከዚህ ውስጥ 141 ሺህ ያህሉ በዚህ ዓመት የተቀላቀሉ አዲስ ተማሪዎች መሆናቸው ተውቋል-(ኤፍ ቢ ሲ)