በሙስሊሙ ማህብረሰብ የሚስተዋሉ መከፋፈሎችን ለማጥበብ የሚያስችል ውይይት ይደረጋል

በሙስሊሙ ማህበረሰብ የሚስተዋሉ መከፋፈሎችንና ልዩነቶችን ለማጥበብ  የሚያስችል ረቂቅ  ሰነድን በማጠናቀቅ በህዝብ ውይይት ለማድረግ መዘጋጀቱን የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ  አስታወቀ ።

ኮሚቴው በዛሬው ዕለት ለመገናኛ ብዙሃን በሠጠው መግለጫ ኮሚቴው ከተቋቋመበት ጊዜ  አንስቶ ያከናወናቸውን ተግባራት ዘርዝሯል ።

ኮሚቴው በመግለጫ የሙስሊሙን አንድነት ዳግም ለመመለስ የተወሰደው የቤት ሥራ  ለመፈጸም ሰፊ ጊዜ መድቦ የተለያዩ  ተግባራትን ሲፈጽም መቆየቱን  አንስቷል ።

ኮሚቴው ከመሥረታው ጀምሮ የተሠጠውን ኃላፊነቱን ለመወጣት እንዲያግዘው እስካሁን  የህግ ጉዳዮችን ፣ የመዋቅር ጥናት፣ የኡለማዎች መግባቢያ ሰነድ ዝግጅትና የገንዘብ አፈላላጊ ንዑሳን ኮሚቴዎች ተዋቅረው ሥራዎችን በሚገባ መወጣታቸው በመግለጫቸው ተመልክቷል  ።

አሁን በተዘጋጀው የኡለማዎች የመግባቢያ ሰነድ መሠረት የመጅሊሱን ፣ የኡላማ ንክር ቤቱንና የአገሪቱን የአስልምና ምክር ቤት አዲስ አቅጣጫ በማመላከት አላስፈላጊ የጭቅጭቅ መድረኮችን የሚያስቀር መሆኑ ተገልጿል ።

በቅርቡ ኮሚቴው በተባበሩት የአረብ ኢምሬቶች የመጅሊሱን አወቃቀርና ሌሎች አሠራሮችን በተመለከተ  ልምድ  ቀስሞ  መምጣቱም  በመግለጫው  ተጠቁሟል ።

በኮሚቴው  የተዘጋጀው ሰነድ  በመጪው ህዳር ወር በተመረጡ  የክልል ከተሞችና ወረዳዎች ውይይት  የሚደረግ መሆኑን  ተገልጿል ።

 ጠቅላይ ሚንስትር ዶክተር  አብይ  ባቀረቡት  ምክር ሓሳብ  መሠረት  ዘጠኝ አባላት  ያሉትን የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ  ሰኔ 26፤ 2010 ዓም መቋቋሙ ይታወሳል ።