አሜሪካ በሚሊየን የሚቆጠሩ ህገወጥ ስደተኞችን ልታባርር ነው

አሜሪካ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ በሚሊየን የሚቆጠሩ ህገወጥ ስደተኞችን ልታባርር መሆኑ ተነገረ፡፡

ኤኤፍፒ ዶናልድ ትራምፕ በትዊተር ገጻቸው ያሰፈሩትን መረጃ ዋቢ አድርጎ እንደዘገበው የሀገሪቱ የስደተኞችና ጉምሩክ ቁጥጥር ባለስልጣን በሀገወጥ መንገድ ገብተው እየኖሩ ያሉ ስደተኞችን በሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ ማባረር ይጀምራል፡፡

የማእከላዊ አሜሪካ አካል የሆነችውና የሜክሲኮ አዋሳኝ ጓቴማላ ለዚሁ ተግባር ከአሜሪካ ጋር ለመስራት ዝግጁ መሆኗን ገልጻለች፡፡

ትራምፕ ስደተኞችን “ወራሪዎች” በማለት አውግዘው አስተዳደራቸው በህወጥ የሚገቡ ስደተኞችን ለመከላከል በትኩረት እንደሚሰራ ገልጸዋል፡፡

አሜሪካ ከጓቴማላና ከሌላው ማእከላዊ አሜሪካ በህገወጥ መንገድ በሚገቡ ስደተኞች የጸጥታ መደፍረስ እያጋጠማት መሆኑንም ዘገባው አመላክቷል፡፡

በአሜሪካና በሜክሲኮ መካከል በተደረገ ስምምነት በደቡባዊ የሃገሪቱ ክፍል እያቋረጡ የሚገቡ ስደተኞችን ለመከላከል 6 ሺህ የጸጥታ አካላትን ልታሰማራ መሆኑንም ነው ዘገባው ያመለከተው፡፡