የኢትዮጵያ ምርት ገበያ በመጋቢት ወር በአጠቃላይ 3ነጥብ 7 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያለው ምርት በመጋቢት ወር ላይ ማገበያየቱን አስታወቀ ።
ምርት ገበያው ለዋልታ በላከው መግለጫ እንዳለመከተው ምርት ገበያው በመጋቢት ወር ፣ 2010 ላይ ባካሄደው ግብይት በአጠቃላይ 3ነጥብ7 ቢሊዮን ብር ዋጋ ያላቸውን ከ72 ሺህ ቶን በላይ የሚሆኑ የተለያዩ ምርቶችን ማገበያየቱን አስታውቋል።
ምርት ገበያው ባደረገው ግብይት የቡና ዋጋ ከፍተኛውን ድርሻ መያዙን አመላክቷል።
በመጋቢት ወር በተካሄደው ግብይት በአጠቃላይ 36 ሺህ 302 ቶን ቡና በ2 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ሲሸጥ 29 ሺህ 215 ቶን ሰሊጥ በ1 ነጥብ 1 ቢሊዬን ብር፣ 4 ሺህ 175 ቶን ቦሎቄ በ64 ሚሊዬን ብር እንዲሁም 2 ሺ 467 ቶን አረንጓዴ ማሾ በ46 ሚሊዮን ብር አገበያይቷል።
ከአጠቃላይ የወርሃ መጋቢት የግብይት ቡና በመጠን 50 በመቶ እንዲሁም በዋጋ 67 በመቶ ሲይዝ፤ ይህም ከየካቲት ወር ጋር ሲነጻጸር የ23 በመቶ በመጠንና 21 በመቶ በዋጋ ጭማሪ ማሳየቱን ነው ምርት ገበያው በላከው መግለጫ ያመላከተው።