46ኛው የሸገር ደርቢ በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ

ሰኔ 18/2015 (ዋልታ) በቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕርሚየር ሊግ 28ኛ ሳምንት ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ያደረጉት የሸገር ደርቢ ጨዋታ 1 ለ 1 በሆነ አቻ ውጤት ተጠናቀቀ።

ፈረሰኞቹን ቀዳሚ ያደረገች ግብ እስማኤል ኦሮ አጎር ሲያስቆጥር ብሩክ በየነ ቡናማዎቹን አቻ ማድረግ ችሏል።

የፈረሰኞቹ የፊት መስመር ተጨዋች እስማኤል ኦሮ አጎሮ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ግቦች 24 አድርሷል፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስ በሊጉ ደረጃ ሰንጠረዥ 60 ነጥቦችን በመሰብሰብ ሊጉን መምራቱን ሲቀጥል ኢትዮጵያ ቡና በ39 ነጥብ 6ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡

በተያያዘ መረጃ ከሀገር ውስጥ ውድድሮች አልፎ በአህጉራዊ እና ዓለም ዐቀፋዊ ውድድሮች ጨዋታዎችን መምራት የቻለችው ዓለም ዐቀፍ ዳኛ ሊዲያ ታፈሠ ዛሬ በአዳማ ሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ስታዲየም በተደረገው ተጠባቂው የሸገር ደርቢ ጨዋታ ከዳኝነት ራሷን አግልላለች፡፡

በጅማ ከተማ የተወለደችው ሊዲያ ታፈሠ 1997 ዓ.ም ጀምሮ በርካታ አህጉራዊ እና ዓለም ዐቀፋዊ የሀገራት እንዲሁም የክለቦች ጨዋታዎችን በብቃት መምራት የቻለች እንስት ዳኛ ነች፡፡

በሀብታሙ ገደቤ