“ሰብአዊነትና ፍቅር ለትግራይና መተከል” በሚል መሪ ሃሳብ ድጋፍ ማሰባሰብ ተጀመረ

“ሰብአዊነትና ፍቅር፤ ለትግራይና መተከል” በሚል መሪ ሃሳብ የድጋፍ ማሰባሰብ መርሃ ግብር ተጀመረ።

የድጋፍ ማሰባሰብ መርሃ ግብሩ መጀመርን አስመልክቶ አስተባባሪ ኮሚቴው ዛሬ መግለጫ ሰጥቷል።

በዚህም ከዚህ ቀደም በአገር ውስጥና በውጭ አገሮች በተናጠል ሆነው የሰብአዊ ድጋፍ ሲያሰባስቡ የነበሩ አካላትን ወደ አንድ ማዕከል በመምጣት “ሰብአዊነትና ፍቅር፤ ለትግራይና መተከል” በሚል መሪ ሃሳብ ድጋፍ ማሰባሰብ መጀመራቸው ተገልጿል።

በአርቲስት እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ ታማኝ በየነ መሪነት ግሎባል አሊያንስ፣ ሰብአዊ ድጋፍ ጥምረት፣ የኢትዮጵያ በጎፈቃደኛ ጋዜጠኞችና የኪነጥበብ ባለሙያዎቸ ለሰብአዊ መብቶች ማህበር፣ ለትግራይ እርዳታ አሰባሰሳብ በጎ ፈቃደኛ፣ ለመተከል እርዳታ አሰባሳቢ በጎ ፈቃደኛ እና የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ከዛሬ ጀምሮ ድጋፍ ማሰባሰብ ጀምረዋል።

የድጋፍ ማሰባሰብ ሥራው በኢትዮጵያ በጣይቱ ሆቴል፣ በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ዋና ጽህፈት ቤት እና በክልል የቀይ መስቀል ቅርንጫፎች ቁሳቁስ የማሰባሰብ ሥራ እንደሚሰራ ተጠቁሟል።

በገንዘብ ድጋፍ የሚያደርጉ በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማህበር ስም በተከፈተ የሒሳብ ቁጥር “10003277016559” ድጋፍ ማድረግ ይችላሉ ተብሏል።

በመላው ዓለም የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንም በግሎባል አሊያንስ በኩል በተከፈተ “በትግራይና መተከል ለተጎዱ ወገኖቻችን የበኩልዎን ይረዱ ዘንድ እናሳሰባለን” በሚል በተከፈተ “ጎ ፈንድ ሚ” አካውንት አማካኝነት ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ ተጠቁሟል።

ኮሚቴው ኢትዮጵያዊነት ከቃል በላይ በተግባርና በአብሮነት የሚገለፅ በመሆኑ በአገር ውስጥም በውጭም የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ከዛሬ የካቲት 2 ቀን 2013 ዓ.ም ጀምሮ የበኩላቸውን ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ ማቅረቡን ኢዜአ ዘግቧል።