በሴፍቲኔት መርሀግብር ታቅፈው ራሳቸውን የቻሉ 170 ሺህ ዜጎች ተመረቁ

መጋቢት 28/2013 (ዋልታ) – በአማራ ክልል በልማታዊ ሴፍቲኔት መርሀግብር ታቅፈው በተደረገላቸው ድጋፍ ራሳቸውን የቻሉ 170 ሺህ ዜጎች መመረቃቸውን የክልሉ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ፕሮግራሞች ማስተባበሪያ ኮሚሽን አስታወቀ።

ኮሚሽኑ 4ኛውን የፕሮግራም ማጠናቀቂያን በማስመልከት የክልልና የዞን ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች በደቡብ ጎንደር ዞን ሁለት ወረዳዎች ባለፉት አምስት ዓመታት የተከናወኑ የልማታዊ ሴፍትኔት እንቅስቃሴን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።

የክልሉ አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘላለም ልጃለም በጉብኝቱ ወቅት እንዳሉት፣ በክልሉ በሚገኙ 70 ወረዳዎች 1 ነጥብ 8 ሚሊየን ዜጎች በሴፍትኔት ፕሮግራም ታቅፈው ከድህነት እንዲወጡ እገዛ እየተደረገ ይገኛል።

ከዜጎቹ ውስጥ 600 ሺህ የሚሆኑት አቅመ ደካሞች፣ በዕድሜ የገፉና የጤና ችግር ያለባቸው በልማት ስራ መሳተፍ የማይችሉ በቀጥታ ድጋፍ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እየተደረደገ መሆኑን ገልፀዋል።

“ባለፉት አምስት ዓመታት ለፕሮግራሙ 10 ነጥብ 4 ቢሊዮን ብር ወጪ በማድረግ ተሳታፊዎቹ ተጨማሪ ሃብት በማፍራት በምግብ ራሳቸውን እንዲችሉ እገዛ ተደርጓል” ብለዋል።

ተሳታፊዎቹ በሚሰጣቸው ብድርና ሌሎች አቅርቦቶች በእንስሳት እርባታ፣ በመስኖ ልማት፣ በአትክልትና ፍራፍሬ፣ በንግድና መሰል ዘርፎች ተሰማርተው ሃብት ማፍራት የቻሉ 170 ሺህ ዜጎች በፕሮግራሙ ተመርቀው ራሳቸውን እንዲችሉ መደረጉን ገልፀዋል ሲል ኢዜአ ዘግቧል።