በተሽከርካሪ ተደብቆ ሲጓጓዝ የነበረ 2,525 ተተኳሽ ጥይት ተያዘ

በህገ ወጥ መንገድ በተሽከርካሪ ተደብቆ ሲጓጓዝ የነበረ 2 ሺህ 525 ተተኳሽ የክላሽ ጥይት መያዙን የፌደራል ጉምሩክ ኮሚሽን ኮምቦልቻ ቅርንጫፍ አስታወቀ።

የቅርንጫፉ የደንበኞች ትምህርትና ስልጠና ቡድን መሪ አቶ አሳምነው አዳነ  እንደገለጹት ተተኳሽ ጥይቱ የተያዘው ትላንት ለሊት በወልዲያ መቆጣጠሪያ ጣቢያ በተደረገ ፍተሻ ነው።

ጥይቱ ከአላማጣ ወደ ባህር ዳር በመጓዝ ላይ በነበረ የሰሌዳ ቁጥሩ ኮድ 3 -06546 አማ በሆነ አይሱዚ የጭነት ተሽከረካሪ በሽንኩርት ውስጥ ተደብቆ ሊያልፍ ሲል በፍተሻ መገኘቱን ተናግረዋል።

ከሌሎች የጸጥታ አካላት ጋር በተደረገ ትብብር አሽከርካሪውን ጨምሮ ሦስት ተጠርጣሪዎች መያዛቸውን አመልክተዋል።

ቅርንጫፉ በህገወጥ መንገድ የሚዘዋወሩ የጦር መሳሪያዎችን የመያዝ ተግባሩን አጠናክሮ መቀጠሉን ቡድን መሪው ማስታወቃቸውን ኢዜአ ዘግቧል።