በግል ትምህርት ቤቶች የኮቪድ መከላከል መመሪያ መተግበሩን ለመመልከት ድንገተኛ ቅኝት ተደረገ

መጋቢት 21/2013 (ዋልታ) – የትምህርት ሚኒስቴር በግል ትምህርት ቤቶች የኮቪድ መከላከል መመሪያ መተግበሩን ለመመልከት ድንገተኛ ቅኝት እያደረገ እንደሆነ ተገለፀ፡፡
የትምህርት ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ በአዲስ አበባ በሚገኙ አንዳንድ የግል ትምህርት ቤቶች በመገኘት የትምህርት ቤቶችን ነባራዊ ሁኔታ ተመልክተዋል።
ምልከታ ከተካሄደባቸው ትምህርት ቤቶች መካከል ሳንፎርድ አለም አቀፍ ትምህርት ቤት እና አሜሪካ ኮሚዩኒቲ ትምህርት ቤት ይገኙበታል።
ሚኒስትር ዴኤታዋ በጉብኝታቸው ትምህርት ቤቶቹ የኮቪድ ወረርሽኝን ለመከላከል እያከናወኑት ያለውን ተግባር ተመልክተዋል፡፡
በወቅቱ የትምህርት ቤቶቹ አስተዳደርም እየተከናወኑ ስላሉ ተግባራት ማብራሪያ መስጠታቸው ተጠቅሷል፡፡
ትምህርት ቤቶቹ የኮቪድ ወረርሽኝን ለመከላከል በትምህርት ሚኒስቴር የተቀመጠውን መመሪያ በአግባቡ መተግበራቸውን በጉብኝታቸው ወቅት መመልከታቸውን ገልፀዋል።
ሌሎች ትምህርት ቤቶችም የኮቪድ ወረርሽን ለመከላከል እና ትምህርት ቤቶች ዳግም እንዳይዘጉ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በትምህርት ቤቶች ውስጥ ሊያደርጉ እንደሚገባ ሚኒስትር ዴኤታዋ አሳስበዋል።
በቀጣይም ትምህርት ሚኒስቴር በትምህርት ቤቶች ድንገተኛ ቅኝት በማድረግ ትምህርት ቤቶች ሚኒስቴሩ ያወጣውን መመሪያ እየተገበሩ መሆኑን እንደሚያጣራ ጠቁመዋል፡፡
እንዲሁም መመሪያውን ባልተገበሩ ትምህርት ቤቶች ላይም አስፈላጊውን እርምጃ እንደሚወሰድ መገለፁን ከትምህርት ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡