ትውልዱ የራሱን አሻራ በማሳረፍ ኢትዮጵያን ማሻገር ይኖርበታል – ወ/ሮ አዳነች አቤቤ

ሚያዝያ 26/2013 (ዋልታ) – ኢትዮጵያን የአፍሪካ ተምሳሌት አድርገው ካቆዩ የአርበኞች ታሪክ ልምድ በመውሰድ የአሁኑ ትውልድም የራሱን አሻራ በማሳረፍ ኢትዮጵያን ማሻገር እንደሚኖርበት የአዲስ አበባ ምክትል ከንቲባ አዳነች አቤቤ ገለጹ፡፡

ምክትል ከንቲባዋ 80ኛው የአርበኞች ቀንን በማስመልከት በአርበኞች ስም የተሰየሙ የራስ ደስታ ሆስፒታል፣ አርበኞች እና የሊሴ ገብረማሪያም ትምህርት ቤቶችን ጎብኝተዋል።

በጉብኝታቸው አርበኞችን ለማስብ ቀን ብቻ ጠብቀን ሳይሆን በየጊዜው ተቋማቱ የተሰየሙበትን አላማ ለትውልዱ ማሳወቅ ያስፈልጋል ብለዋል።

አባት አርበኞች  ወራሪውን በመመከት የኢትዮጵያን አንድነት  ጠብቀው  አስረክበውናል ያሉት ምክትል ከንቲባዋ፣ የአሁኑ ትውልድም የሀገርን አንድነት ጠብቆ የአባቶቻችንን ታሪክ በልማቱም በመድገም ኢትዮጵያን ለማሻገር የራሱን አሻራ ለማሳረፍ ጥረት ማድረግ እንደሚገባው ማሳሰባቸውን ከአዲስ አበባ ፕሬስ ሴክሬቴሪያት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።