አሸባሪው ህወሓት ከ170 በላይ እርዳታ የጫኑ ከባድ መኪናዎችን አግቶ ማቆሙን የትራንስፖርት ሚኒስትሯ አስታወቁ

ሐምሌ 21/2013(ዋልታ) – አሸባሪው ህወሓት ከ170 በላይ እርዳታ የጫኑ ከባድ መኪናዎችን አግቶ ማቆሙን የትራንስፖርት ሚኒስትር ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ  አስታወቁ።

የትራንስፖርት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ እንዳስታወቁት ወደ ትግራይ ሊጓጓዝ የተጫነን የእርዳታ እህል የያዙ 170 ከባድ ተሽከርካሪዎች በአሸባሪው ህወሓት አማካኝነት ጉዟቸው ተገትቶ ቆመዋል።

በተመሳሳይ የዓለም የምግብ ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዴቪድ ቤዝሌይ በትግራይ ያለው የእርዳታ ምግብ ክምችት የፊታችን አርብ ያልቃል ሲል ዛሬ አስታውቋል።

በክልሉ እርዳታ የሚፈልገውን እያንደንዱን ሰው ለመድረስ በቀን እስከ መቶ ተሽከርካሪ የሚደርስ ምግብ ያስፈልጋል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ምግብ የጫኑ 170 ተሽከርካሪዎች አፋር ላይ ታግተው መንቀሳቀስ አልቻሉም ብለዋል።

እነዚህ ተሽከርካሪዎች ሊለቀቁ ይገባል ያሉት ዳይሬክተሩ፤ ሰዎች እየተራቡ ነው ሲሉም አስታውቀዋል።

መንግስት አሁን የዓለም የምግብ ድርጅት ይህን ከማስታወቁ ከሣምንታት በፊት አሸባሪው ህወሓት ወደ ትግራይ ክልል የሚገቡ እርዳታ የጫኑ ተሽከርካሪዎችን አግቶ ማስቆሙን ማስታወቁ ይታወሳል።

መንግሥት የተናጠል የተኩስ አቁም ውሳኔን አሳልፎ የትገራይ ክልልን ጥሎ ሲወጣ  ከአራት ሚሊዮን በላይ  ተረጂዎችን የሚቀልብ እህል ትቶ መውጣቱን፤ እንዲሁም መድሃኒት እና ነዳጅም ትቶ መውጣቱን ማስታወቁ ይታወሳል።

ከዚህ በተቃራኒ የጁንታው አፈቀላጤ ጌታቸው ረዳ ልጁን ለጦርነት ያልሰጠ ቤተሰብ የእርዳታ እህል እንዳይሰጠው የሚል መመሪያ ማውረዱን ተከትሎ፤ ከስር ያሉ ካድሬዎች ይህንን ለማስፈጸም በሚያደርጉት ርብርብ ከህዝብ ጋር ከፍተኛ ግጭት ውስጥ እየገቡ  መሆናቸውን ኢፕድ ዘግቧል።