ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ ነው

ግንቦት 22/2014 (ዋልታ) ከውጭ አገር ከተገዛው የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ ከ8 ሚሊዮን ኩንታል በላይ ማዳበሪያ ሀገር ውስጥ ተጓጉዞ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን የኢትዮጵያ የግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን ገለጸ።

ኮርፖሬሽኑ ለ2014/15 የሰብል ምርት ዘመን 12 ሚሊዮን 876 ሺሕ 623 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ከውጭ ገዝቻለው ብሏል።

ከዚህ ውስጥ ከጥር ወር ጀምሮ እስከ ግንቦት 22 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ 9 ሚሊዮን 829 ሺሕ 190 ኩንታል የአፈር የተለያዩ ማዳበሪያ አይነቶች ጅቡቲ ወደብ መድረሳቸውን ገልጿል።

ከዚህም 8 ሚሊዮን 243 ሺሕ 689 (84 በመቶው) ወደ ሀገር ውስጥ ተጓጉዞ ለአርሶ አደሩ እየቀረበ መሆኑን የኮርፖሬሽኑ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊው ጋሻው አይችሉህም ተናግረዋል።

ለዘንድሮ የሰብል ዘመን ከሞሮኮው የአፈር ማዳበሪያ አምራች ኩባንያ ኦ ሲ ፒ (OCP) የተገዛው የ ኤን ፒ ኤስ (NPS) አይነት ማዳበሪያ ወደ ጅቡቲ ወደብ የማጓጓዝ ሥራ ሙሉ በሙሉ ተጠናቋል ብለዋል።

በሌላ በኩል ከውጭ ሀገር ከተገዛው 5 ሚሊዮን 1 ሺሕ 100 ኩንታል ዩሪያ የአፈር ማዳበሪያ ውስጥ በአራት ዙር ጅቡቲ ወደብ የተራገፈው የዩሪያ የአፈር ማዳበሪያ መጠን 1 ሚሊዮን 953 ሺሕ 670 ኩንታል (39 በመቶ) ደርሷል ነው ያሉት።

ከሁለት ቀን በኋላ ተጨማሪ 450 ሺሕ ኩንታል ዩሪያ ወደብ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አብራርተዋል።

ኮርፖሬሽኑ ለዘንድሮ የሰብል ዘመን የገዛው 12 ሚሊዮን የአፈር ማዳበሪያ ኦሲ ፒ እና ፈርቲ ግሎብ ከተሰኙ ዓለም አቀፍ የአፈር ማዳበሪያ አምራች ኩባንያዎች ነው የገዛው።
ለዘንድሮ የሰብል ዘመን ከሞሮኮው ኦ ሲ ፒ ኩባንያ የተገዛው 7 ሚሊዮን 875 ሺሕ 523 ነጥብ 4 ኩንታል ኤን ፒ ኤስ (NPS) የአፈር ማዳበሪያ አይነት በ13 መርከቦች ተጓጉዞ ሙሉ በሙሉ ጅቡቲ ወደብ ደርሷል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት ባለፈው ሣምንት የመጨረሻዋ መርከብ ያራገፈችው ኤን ፒ ኤስ እና ኤን ፒ ኤስ ቢ ማዳበሪያ ወደ ሀገር ውስጥ እየተጓጓዘ መሆኑን ኮርፖሬሽኑን መረጃ ጠቅሶ ኢዜአ ዘግቧል።