የሚኒስትሮች ምክር ቤት ባካሄደው መደበኛ ስብሰባ ውሳኔዎችን አሳለፈ

መጋቢት 25/2016 (አዲስ ዋልታ) የሚኒስትሮች ምክር ቤት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 28ኛ መደበኛ ስብሰባ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ አሳለፈ፡፡

28ኛ መደበኛ የሚኒስትሮች ምክር ቤት ስብሰባ ውሳኔዎች:-

1. በቅድሚያ ምክር ቤቱ የተወያየው የመካከለኛ ዘመን 2017-2021 የማክሮ ኢኮኖሚ እና ፊሲካል ማዕቀፍ ላይ ነው፡፡ የማክሮ ኢኮኖሚና ፊሲካል ማዕቀፉ የመንግስት በጀት ከማክሮ ኢኮኖሚ ሁኔታው እና የፊሲካል አቅም ጋር ተጣጥሞ እንዲዘጋጅ ለማድረግ፤ ከመንግስት ገቢ አሰባሰብ እና ሀብት አመዳደብ አኳያ የፖሊሲ አቅጣጫዎችን በማመላከት ለቀጣይ በጀት አመት የበጀት ዝግጅት ለማድረግ፤ የመካከለኛ ዘመን የመንግስት ገቢና ወጪ እንዲሁም የፊሲካል ሚዛን የፖሊሲ አቅጣጫዎችን ለመለየት እና ለማመላከት የሚያገለግል ማዕቀፍ በመሆኑ ምክር ቤቱ በሰፊው ከተወያየበት በኋላ በስራ ላይ እንዲውል በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡

2. በመቀጠል ምክር ቤቱ የተወያየው የተጨማሪ እሴት ታክስ ረቂቅ አዋጅ ላይ ነው፡፡ የተጨማሪ እሴት ታክስ ስራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ በሀገሪቱ የእኮኖሚ እንቅስቃሴ ውስጥ የተደረጉ ለውጦችን በህግ ማእቀፉ ውስጥ ማስገባት በማስፈለጉ፣ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች የተጨማሪ እሴት ታክስ ጫና እንዳያርፍባቸው ለማድረግ የሚያስችል ረቂቅ አዋጁ ተዘጋጅቶ ለሚኒስትሮች ምክር ቤት ቀርቧል፡፡ ምክር ቤቱም በረቂቅ አዋጁ ላይ በሰፊው ከተወያየበት በኋላ ግብዓቶችን በማከል ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንዲተላለፍ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡