የሳዑዲ ዓረቢያው ዲዘርት ቴክኖሎጅስ ኩባንያ በኢትዮጵያ በፀሐይ ኃይል ሊሰማራ ነው

መጋቢት 23/2013 (ዋልታ) – የሳዑዲ ዓረቢያው ዲዘርት ቴክኖሎጅስ ኩባንያ በኢትዮጵያ በፀሐይ ኃይል የሚሰሩ መሣሪያዎችን የማምረት ፍላጎት እንዳለው አስታወቀ፡፡
የኩባንያው አመራሮች በኢትዮጵያ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በኢትዮጵያ በታዳሽ ኃይል ኢንቨስትመንት ዙሪያ ተወያይተዋል፡፡
ውይይት የተካሄደው ባለፈው ዓመት የኩባንያው ተወካዮች በአዲስ አበባ ያካሄዱትን የቅድመ-ኢንቨስትመንት የመስክ ጉብኝት ተከትሎ ነው ተብሏል፡፡
ውይይቱ በዋናነት በኢትዮጵያ የሙከራ ጣቢያዎችን ለማቋቋምና ከፀሐይ ኃይል የሚያመነጩ የተለያዩ መሣሪያዎችን መስራት በሚቻልበት አግባብ ላይ ያተኮረ ነበር ተብሏል፡፡
የውሃ፣ ኤሌክትሪክ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ሶስት የፕሮጀክት ቦታዎችን የሚመርጥ ሲሆን፥ ኩባንያውም ወደ ስራ ለመግባት የገንዘብ ምንጮችን ያፈላልጋል መባሉን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።