የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ በህዳሴ ግድብ አካባቢ ሆቴል ሊገነባ ነው

 

 

የካቲት 25 /2013 (ዋልታ) – የአሶሳ ዩኒቨርሲቲ የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሲጠናቀቅ የሚፈጠረውን የጎብኚዎች ከተማ ተከትሎ በአካባቢው የራሱን ሆቴል እንደሚገነባ አስታወቀ።

የአሶሳ ዩኒቨርሲቲፕሬዚዳንትአቶ ከማል አብዱራሂም ÷ ዩኒቨርሲቲው የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ሲጠናቀቅ የሚፈጠረውን የጎብኚ ከተማ ተከትሎ በአካባቢው የራሱን ሆቴል ለመገንባት በ10 አመት መሪ እቅዱ ውስጥ አካቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል።

ክልሉ ከቱሪዝም አኳያ እምቅ ሀብት ያለው መሆኑን የጠቆሙት አቶ ከማል÷ ዩኒቨርሲቲው በቅድሚያ በክልሉ የሚገኙ የባህልና የቱሪዝም ሃብቶችን የማስተዋወቅ ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።

ከእነዚህ ውስጥም የበርታ ብሄረሰብ የሚጠቀምበት ̎ዙምባራ ̎ የተሰኘውን የትንፋሽ ሙዚቃ መሳሪያ የክልሉ አንድ መለያ መሆኑን በመለየት አስመዝግቦ ጥናት እንዲካሄድበት እያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል።

በክልሉ ያሉ የሌሎች ብሄረሰቦችን ባህላዊ መሳሪያዎቻቸውን ለማስተዋወቅ ተመሳሳይ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ አስታውቀዋል።

ከክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮና ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ጋር በመሆን በክልሉ የሚገኙ የመስህብ ስፍራዎችን መሰረተ ልማት የሌላቸው እንዲኖራቸው የማድረግ ስራዎች ይሰራሉ ማለታቸውን ኢፕድ ዘግቧል።