የአገልግሎቱ መረጃዎች ለፀጥታ አካላት ስምሪት አስቻይ ሁኔታን በመፍጠር የሀገሪቱ ፀጥታ እንዲሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከታቸው ተገለጸ


መጋቢት 13/2016 (አዲስ ዋልታ) የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ያመነጫቸው መረጃዎች ለፀጥታ አካላት ስምሪት አስቻይ ሁኔታን በመፍጠር የሀገሪቱ ፀጥታ እንዲሻሻል ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከታቸው ተገለጸ።

አገልግሎቱ የ2016 በጀት ዓመት የስድስት ወራት ዕቅድ አፈጻጻም የተቋሙ ዳይሬክተር ጀነራል አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን በመሩት መድረክ ተገምግሟል።

አገልግሎት ለአዲስ ዋልታ በላከው መረጃ እንዳመለከተው በበጀት ዓመቱ ስድስት ወራት የሀገርን ደኅንነት የሚያስጠብቁ መረጃዎችን በማመንጨት እና ለፈፃሚ አካላት በማቅረብ ረገድ ውጤታማ ሥራዎች ተከናውነዋል።

በተለይ በአማራ እና ኦሮሚያ ክልሎች ያሉትን የፀጥታ ችግሮች ከመቅረፍ አኳያም የመረጃና የኦፕሬሽን ድጋፍ በመስጠት ከፍተኛ አስተዋጽዖ ማበርከት ተችሏል። የአፍሪካ ሕብረትን ዓመታዊ ጉባኤን ጨምሮ ሌሎችም ሃይማኖታዊና ባሕላዊ ሁነቶች በስኬት እንዲጠናቀቁም ተቋማዊ ሚናውን በላቀ ስኬት ተወጥቷልም ነው የተባለው፡፡

የአገልግሎቱ የተልዕኮ ሥራዎች ውጤታማነት በሀገር ደኅንነት ከባቢ ላይ ከሚያሳድሩት ተፅዕኖ አንጻር መለካት እንዳለባቸው በመድረኩ መነሳቱን ያመለከተው መረጃው በዚህ ረገድ በስድስት ወራት ውስጥ የተከናወኑ ተግባራት ውጤት የተገኘባቸው መሆናቸው ተገምግሟል።

በዚህም ለፀጥታ አካላት አስቻይ ሁኔታዎችን በመፍጠር የሀገሪቱ የፀጥታ ሁኔታ በአንጻራዊነት እንዲሻሻል አገልግሎት መሥሪያ ቤቱ ከፍተኛ አስተዋፅዖ አበርክቷል።

አገልግሎቱ መረጃ የመሰብሰብ እና የመፈጸም አቅም በመጨመሩ ምክንያት እንዲሁም ከሌሎች የፀጥታ አካላት ጋር በቅንጅት የመሥራት ባሕሉ በመጠናከሩ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ይታዩ የነበሩ የፀጥታ ችግሮች እየተሻሻሉ መምጣታቸው ተጠቁሟል፡፡

ዕቅዱ ሀገሪቱ ካለችበት የፀጥታ ሁኔታ አንጻር እንዲሁም በቀጣናው ያለው የደኅንነትና የፖለቲካ ሁኔታ ውስብስብ እየሆነና እየተባባሰ በሚገኝበት አውድ የተፈጸመ ከመሆኑ አንፃር ስኬታማ ነበር ማለት እንደሚቻል ተመላክቷል።

የአገልግሎቱን የመፈጸም አቅም ለማሳደግ በሰው ኃይል ሥልጠና፣ በቴክኖሎጂ፣ በሎጀስቲክስ እና ምቹ የሥራ አካባቢን በመፍጠር ረገድም ሰፋፊ ሥራዎች መሠራታቸውም ተገልጿል።

የሀገር ውስጥም ሆነ የውጭ አጋርና አቻ ተቋማት ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ጋር በትብብር ለመሥራት ከፍተኛ ፍላጎት እያሳዩ መምጣታቸው የአገልግሎቱ የመፈጸም አቅምና የተጽዕኖ አድማስ እየሰፋ መምጣቱን ያሳያል ያለው መረጃው በቀጣይም ይህን አዎንታዊ ተጽዕኖ ለማጎልበት ስትራቴጂያዊ በሆኑ ተልዕኮዎች ላይ ትኩረት እንደሚደረግ ገልጿል።

አገልግሎቱ መረጃዎችን የማመንጨትና ትንበያዎችን የማስቀመጥ አቅሙ በማደጉ በቀጣናው ከሚታዩት ፈጣንና ተለዋዋጭ የደኅንነት ሁኔታዎች አንፃር ብሔራዊ ደኅንነትንና ጥቅምን የሚያስጠብቁ ስምሪቶች ከማከናወን ባሻገር ከተለያዩ ሀገራት አቻ ተቋማት ጋር በትብብር የመሥራት ሂደቱ እየጨመረ መምጣቱ በመረጃው ተመልክቷል።

በዚህም ሽብርተኝነትን፣ ሕገወጥ የጦር መሣሪያና የሰዎች ዝውውርን እንዲሁም ድንበር ዘለል ወንጀሎችን በጋራ ለመከላከል ተችሏል፡፡

በቀጣይም በህብረተሰቡ ውስጥ የሚፈፀሙ የውንብድና ወንጀሎችን ተከታትሎ መረጃ በማጥራትና በማጠናቀር ከሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ጋር በመሆን እርምጃ እንዲወሰድ የሚያስችሉ ስምሪቶች እንደሚከናወኑ ተመልክቷል።

በሀገር ውስጥ ያለውን የፀጥታ እና ደኅንነት ሁኔታ አስተማማኝ ለማድረግም ፖለቲካዊ መፍትሄዎችን የሚያመጡና ተጽዕኖ የሚፈጥሩ መረጃዎችን ማምረት ላይ ትኩረት እንደሚደረግም ተጠቁሟል።

የኢኮኖሚ አሻጥር በተለይ የሀብት ሽሽት ላይ እንዲሁም ከኤርፖርት አገልግሎት አሰጣጥ ጋር በተያያዘ ከተቋሙ የተልዕኮ ማዕቀፍ አንጻር አስተማማኝ የደኅንነት ሁኔታ እንዲሰፍንና የተገልጋዮች ቅሬታ እንዳይፈጠር የሚያስችሉ ተግባራት ትኩረት ተሰጥቷቸው እንደሚሠሩ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት በላከልን መረጃ አመልክቷል።