ዲያስፖራዎች በአሸባሪው ትሕነግ የወደመውን ለመተካት የሚደረገውን እንቅስቃሴ እናግዛለን አሉ

ጥር 2/2014 (ዋልታ) በአሸባሪው ትሕነግ የደረሰውን ቁሳዊ ውድመት ለመተካት የሚደረገውን እንቅስቃሴ እንደሚያግዙ ወደ አገር ቤት የገቡ ዲያስፖራዎች አስታወቁ።

አሸባሪው ትሕነግ በአማራ ክልል ያደረሰውን ሰብኣዊና ቁሳዊ ውድመት የሚያሳይ የፎቶ ዐውደ ርዕይ በባሕር ዳር ከተማ ተከፍቷል።

ዐውደ ርዕዩን የጎበኙ ዲያስፖራዎች አስተያየታቸውን ለኢዜአ ሲሰጡ የትሕነግ የጭካኔ ጥግ ምን ያህል የከፋ መሆኑን መረዳት መቻላቸውን ገልጸዋል።

ወደሚኖሩበት አገር ሲመለሱም የደረሰውን የጉዳት መጠን ለኢትዮጵያዊያንና ትውልደ ኢትዮጵያዊያን የማስገንዝብ ሥራ እንደሚሰሩ አመላክተዋል።

በሽብር ቡድኑ ለወደመው ሃብትና ንብረት በቁጭት በመነሳሳት ድጋፍ እንደሚያደርጉ ተናግረዋል። ንብረቱን በአጭር ጊዜ ውስጥ መተካት እንደሚገባም ጠቁመዋል።