2ኛው ዙር የውሃ ሙሌት በተያዘለት ጊዜ ይከናወናል – ዶ /ር አረጋዊ በርሄ

ግንቦት 30/2013 (ዋልታ) – የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሁለተኛ ዙር የውሃ ሙሌት በተያዘለት ጊዜ እንደሚከናወን ዶክተር አረጋዊ በርሄ ገለፁ፡፡

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ግንባታ ህዝባዊ ተሳትፎ ማስተባበሪያ ብሄራዊ ምክር ቤት ጽ/ቤት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር አረጋዊ በርሄ የግድቡ ግንባታ በተቀመጠው የጊዜ ሰሌዳ መሠረት ያለምንም ችግር እየተካሄደ መሆኑን ለዋልታ ገልጸዋል፡፡

ኢትዮጵያውያን በቦንድ ግዢ፣ በ8100A አጭር የጽሑፍ መልእክት እያደረጉት ባለው የማያቋርጥ ንቁ ተሳትፎ 20 ቢሊዮን ብር መሰብሰቡን ዳይሬክተሩ ተናግረዋል::

የአሜሪካን መንግስት በኢትዮጵያ የመንግስት ከፍተኛ ባለስልጣናት እና የፀጥታ ኃይሎች ላይ የጣለውን የቪዛ እገዳን በተመለከተ አሜሪካ የኢትዮጵያ መንግስት ከህወሃት አሸባሪ ቡድን ጋር ለድርድር እንዲቀርብ ኢ-ፍትሃዊ ጫና እያሳደረ ነው ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያ እና አሜሪካ 120 ዓመት ያስቆጠረ የሁለትዮሸ ግንኙነት ቢኖራቸውም፣ የሽብር ቡድኑን ወደ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ለመመለስ ማሰባቸው ተቀባይነት የለውም ነው ያሉት፡፡

ኢትዮጵያውያን የውስጥ ልዩነቶችን በማጥበብ ለጋራ ብልጽግና በአንድነት እንዲቆሙም ዶ/ር አረጋዊ አሳስበዋል፡፡

የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ የኃይል ማስተላለፊያ መሥመር ዝርጋታ ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀ ሲሆን አጠቃላይ የግድቡ ግንባታ 80 በመቶ ደርሷል፡፡
(በትዝታ መንግስቱ)