በአርብቶ አደር ልማት ፕሮጀክቱ ከ 2 ነጥብ 9 ሚሊዮን በላይ አባውራዎችና እማውራዎች ተጠቃሚ መሆናቸው ተገለጸ

አዲስ አበባ ፤ ጥቅምት 12 ፤ 2006 (ዋኢማ) – በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር እየተከናወነ ባለው የአርብቶ አደር ልማት ፕሮጀክት 2ነጥብ 98 ሚሊዮን የሚሆኑ አባውራና እማውራ አርብቶ አደሮች  ተጠቃሚ  መሆናቸውን  የፌደራል ጉዳዮች  ሚኒስቴር  ገለጸ ።

በፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር የአርብቶ አደር ማህብረሰብ ልማት ፕሮጀክት ተጠባባቂ አስተባባሪ አቶ ሰይድ ዑመር ለዋልታ እንደገለጹት በጥር 2001 ዓም የተጀመረው የአርብቶ አደሩን ያሳተፈው የልማት ፕሮጀክት እስካሁን  በመጠጥ ውሃ ፤ በእንስሳት እርባታ ፤በትምህርት ፤ በሰውና በጤና ኬላዎች ፤  በመንገድና የመስኖ ልማት ዘርፎች  2 ነጥብ 9 ሚሊዮን የሚሆኑ የአርብቶ አደሩ አባውራዎችና አማውራዎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ አስችሏል ብለዋል።

በአርብቶ አደሩ ልማት ፕሮጀክት በአፋር ፤ ጋምቤላ ፤ቤኒሻንጉል ፤ ሶማሌና አርብቶ አደር ባለባቸው  የኦሮሚያና የደቡብ ክልሎች ተግባራዊ እየተደረገ  መሆኑን የገለጹት  አቶ ሰኢድ  በታህሳስ  ወር 2006 ዓም የሚጠናቀቀው ሁለተኛው የፕሮጀክቱ መርሃግብር  55 ወረዳዎች  ያካተተ መሆኑንና  እስካሁን 1 ነጥብ 49 ቢሊዮን ብር ወጪ መደረጉን አያይዘው ተናግረዋል ።

በአርብቶ  አደሩ የቁጠባ ባህልን እንዲያጎለብት ከፌደራል ሕብረት ሥራ ኤጀንሲ ጋር በመተባበር  29 ሺ 441 አባላት ያሉት  448 የብድርና ቁጠባ ተቋማት   19ነጥብ 3 ሚሊዮን  ብር ቆጥበዋል ያሉት  አቶ ሰይድ  የአርብቶ አደሩን  ያኗኗር  ዜይቤ  እየተቀረ  መምጣቱን የጠቆመ ነው ብለዋል ።

በተለያዩ አካባቢዎች  የሚኖሩ አርብቶ አደሮች ያላቸውን ምርጥ ተሞክሮ በመቀመር ሌሎች  አርብቶ  አደሮች  እንዲጠቀሙበት ለማስቻል የልምድ ልውውጥ በየጊዜው  እንደሚከናወን የጠቀሱት አቶ ሰይድ  አንዱ ከሌላው እንዲማር ማገዙን ገልጸዋል ።

በፌደራል  ሚኒስቴር ሥር በሚከናወነው  የአርበቶ አደር ማህበረሰብ ልማት ፕሮጀክት በ ሶስት አምስት  ዓመታት ተከፋፍሎ ለ 15 ዓመታት የሚካሄድ  ሲሆን  ሶስተኛው መርሃ ግብር  በጥር  2006  እንደሚጀመርና   ከአለም ባንክ ና ከአለም አቀፍ የግብርና ልማት ፈንድ ቃል በተገባ  የብድር  ገንዘብ  ለማከናወን መታቀዱን  ዋልታ ኢንፎርሜሽን ማዕከል ዘግቧል ።