አንድነትን የሚሰብኩ ስራዎች ለማበርከት የቤት ስራ ወስደናል-የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች

የአገር ፍቅርና የአንድነት አስተሳሰቦችን በህብረተሰቡ ውስጥ ለማስረፅ የሚያስችሉ ተግባራት ለመከወን የቤት ሥራ መውሰዳቸውን የኪነጥበብ ሙያተኞች ገለፁ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ትናንት ከኪነጥበብ ባለሙያዎች ጋር ተወያይተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ እስካሁን የአገር አንድነትን እና አብሮነትን ለማጉላት ጥረት እያደረጉ ለሚገኙት የኪነጥበብ ሰዎች ያላቸውን አክብሮት በውይይቱ ላይ ገልጸዋል።

አስተያየታቸውን የሰጡ የኪነጥበብ ባለሙያዎች እንደተናገሩት በውይይቱ ላይ የተነሱ ሀሳቦች የኪነጥበብ ሙያተኞች ለአገር ሰላምና ዕድገት መጫወት የሚጠበቅባቸውን ሚና ለማጎልበት የሚያግዝ ነው።

አርቲስት ደሳለኝ ኃይሉ ውይይቱ ስኬታማና የተነሱ ሃሳቦችም የኪነጥበብ ባለሙያዎች በተሰማሩበት ዘርፍ ያላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያጎለብቱ የሚያግዝ ነው ብሏል።

የኪነጥበብ ባለሙያው በማንኛውም አገራዊ፣ ፖለቲካዊና ማህበራዊ ችግሮች ዙሪያ መፍትሄ ሊሆኑ የሚችሉ አጋዥ ሀሳቦችን ለማመንጨት አቅም ያለው መሆኑ የተብራራበት እንደሆነም ገልጿል።

ዘርፉ በተለይም ይቅርታንና ስነምግባርን በተመለከተ የህብረተሰቡን አመለካከት ለመግራት ትልቅ መሳሪያ እንደሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተናገሩት መሰረት ሙያተኛው የድርሻውን ለመወጣት ዝግጁ ነውሲል አርቲስት ደሳለኝ ተናግሯል።

በውይይቱ የኪነጥበብ ሙያተኛው የአገራዊ አንድነትንና መደመርን የሚሰብኩ ሥራዎችን ለህብረተሰቡ በማቅረብ አገሪቱን ወደላቀ ደረጃ ለማድረስ የሚደረገውን ጥረት ለማገዝ የበኩሉን እንዲወጣ የቤት ሥራ የተጠሰው መሆኑንም አክሏል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር ዋና ስራ አስኪያጅ አርቲስት ነብዩ ባዬ በበኩሉ በአሁኑ ወቅት ለህዝበ እየቀረቡ ባሉት የፊልምና ቴአትር ሥራዎች ኢትዮጵያ ከመግለጽ አኳያ ክፍተት እንዳለባቸው በውይይቱ መነሳቱን ጠቁሟል።

ውይይቱ የኪነጥበብ ዘርፉየኢትዮጵያዊነትትክክለኛ ገፅታና ስሜትን ከመግለጽ አኳያ ወደፊት በስፋት ሊሰሩ በሚገባቸው ቁም ነገሮች ላይ ትኩረት የተሰጠበትና ሙያተኛውም በነጻነት እንዲንቀሳቀስ ምቹ ሁኔታዎች እንዲኖሩ ዕድል የፈጠረ ነው ሲልም ተናግሯል።

በአጠቃላይ ውይይቱ የኪነጥበብ ሥራዎች የህዝቡን ችግር በማንሳት መፍትሄ እንዲመጣና ያልታዩ ጉዳዮችን በመዳሰስ አዳዲስ የፈጠራ ሥራዎች ለመጀመር ስንቅ ሆኖናልበማለት ነው አርቲስት ነብዩ የገለፀው።

በአገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች ተከስቶ የነበረውን ግጭት ለማረጋጋት የኪነጥበብ ባለሙያው የሚጠበቅበትን ሚና አለመጫወቱ አሉታዊ ተጽእኖ አሳድሯልየሚል ሀሳብ በጠቅላይ ሚኒስትሩ መነሳቱን የገለጸው ደግሞ ገጣሚ ታገል ሰይፉ ነው።

የኪነጥበብ ባለሙያው እነዚህን በመሳሰሉ አገራዊ ጉዳዮች ላይ በድፍረት በመስራት ስሜቱን መግለጽ እንደሚችል መገለጹን የተናገረው ታገል ሰይፉ በዚያው ልክ የአንድነትንና አብሮነት አስተሳሰቦችንም ለማጎልበት መትጋት እንደሚገባ አጽንኦት ተሰጥቶታል ብሏል።

ትውልዱን በተሟላ ስብእና ለመቅረጽ ከወላጆች በተሻለ የኪነጥበብ ባለሙያው መዋእለህጻናት ድረስ በመውረድ ጭምር በሙያው ትውልዱን ሊያንጽ ይገባል በተባለው መሰረትም የድርሻችንን እንወጣለን ብለን ተግባብተናልብሏል።

የፊልምና የቴአትር ባለሙያው አርቲስት ዳንኤል ተገኝ በበኩሉ መጤ ባህልን ከማስቀረት አኳያ በተለይም ወጣቱ አገር ወዳድና ለአገሩ ተቆርቋሪ እንዲሆን የኪነጥበብ ባለሙያው የድርሻውን መወጣት ላይ በስፋት ሊሰራ እንደሚገባ በውይይቱ መነሳቱን ጠቁሟል።

የቀድሞ የኪነጥበብ ባለሙያዎች ያበረከቷቸው ሥራዎች አሁንም የሚወሱ በመሆናቸው የአሁኑ ትውልድና የዘርፉ ባለሙያዎችም የቆዩትን አርአያ በመከተል የማይረሱ ስራዎችን ማበርከት እንደሚገባ ከመድረኩ መነሳቱን አውስቷል።

ውይይቱ ኪነጥበብ በሁሉም ዘርፍ ገንቢ ሚና መጫወት የሚችል አቅም ያለው መሆኑ የተወሳበት መሆኑን አስተያየት ሰጪዎቹ ተናግረዋል።

ባለሙያውም ያለበትን ክፍተት እንዲያይም አድርጎታል ብለዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ የኪነጥበብ ባለሙያዎችን ሰብስበው ማነጋገራቸው ሁሉም ሙያተኛ የቤት ስራን እንዲወስድና በተግባርም እንዲወጣ ያነሳሳው መሆኑንም ነው ሙያተኞቹ የገለፁት።(ኢዜአ)