ፍርድ ቤቱ በአብዲ ኡመርና ሌሎች የሥራ ኃላፊዎች ላይ ፖሊስ የጠየቀውን የ14 ቀናት የምርመራ ጊዜ ፈቀደ

የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት በዛሬው ዕለት ባካሄደው 4ኛ የወንጀል ውሎው ፖሊስ በእነ አብዲ ኡመርና  ሌሎች የሶማሌ ክልል  የሥራ ኃላፊዎች  ክስ መዝግብ ላይ  የጠየቀውን  የ14  ቀናት ተጨማሪ  ምርመራ ጊዜ  ፈቅዷል ።

በሶማሌ ክልል ከሐምሌ  26  እስከ 30  2010 ድረስ  በተፈጠረው  ሁከት   ምክንያት  በግለሰቦች  ንብረት 741  ሚሊዮን ብር  የሚገመት  ንብረት ተጠርጣሪዎች  እንዲወድም  ማድረጋቸውን ፖሊስ  መረጃዎችን ማጠናከሩን በችሎቱ ገልጿል ።

የፌደራል ፖሊስ  የምርመራ ቡድን በሶማሌ ክልል  በተፈጠረው ሁከትና ብጥብጥ ጋር በተያያዘ  የተለያዩ ሰዎችን የቃል ምስክርነት ተቀብሏል  ።

በተጨማሪም ከተጠርጣሪዎች  ጋር በተያያዘ የተገኙ የጽሑፍ መረጃዎች ከሶማሌኛ ወደ አማርኛ  እንዲተረጎሙ ማድረጉን ፖሊስ  ገልጿል ። 

መርማሪ ፖሊስ  አጠቃላይ  የምርመራ ውጤቶች  ለመጠበቅ ፣የቀሩ ሥራዎችን ለማከናወን  ፣  የምስክር  ቃል  ለመቀበል  ፣ የወንጀል ግብር አበሮችን  ለመያዝና የአስከሬን ምርመራ  ውጤትን  ለማመሳከር ተጨማሪ  የ14  ቀናት ጊዜ  እንዲሠጠው  ፍርድ ቤቱ   የጠየቀ  ሲሆን ፍርድ ቤቱ ፈቅዷል ።