በአስመራ ከተማ ትናንት በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ 28 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

በትናንትናው ዕለት በኤርትራ መዲና  አስመራ  በተካሄደው ሰላማዊ ሰልፍ 28 ሰዎች  በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸው  የተለያዩ  የዜና አውታሮች   እየዘገቡ  ይገኛሉ ።

የአገሪቱ  የተቃዋሚ ኃይሎች ፣ ዓለም አቀፍ  የሰብዓዊ  መብት  ተከራካሪዎች ድርጊቱን   እጅግ አሳሳቢ  መሆኑን  እየገለጹ ነው ።

በኤርትራ ዋና ከተማ አስመራ  የሚገኘው የአሜሪካ ኢምባሲ ማክሰኞ ዕለት  በአስመራ  ከተማ በተካሄደው  የተቃውሞ ሰላማዊ  ሰልፍን  ተከትሎ የአሜሪካ  ዜጎች ወደ  ኤርትራ  ጉዞ  እንዳያደርጉ የማስጠንቀቂያ መልዕክት  ማስተላላፉ  ይታወሳል    ኢምባሲው ባወጣው ጽሑፍ እንዳስታወቀውም  በአስመራ ከተማ  የተኩስ  ድምጽ  መሰማቱንና በተለይ ተቃውሞ ባለባቸው አካባቢዎች የአሜሪካ ዜጎች  እንዳይንቀሳቀሱ ጥሪ አቅርቧል ።        

የቀይ ባህር አፋር ዴሞክራሲያዊ  ድርጅት በማህበራዊ ትስስር ገጹ ላይ  እንደጻፈው  “ በትናንትናው  ዕለት በአሥመራ ከተማ  በተካሄደው  የተቃውሞ ሰልፍ   28  ዜጎች  ህይወታቸውን መስዋዕት  ማድረጋቸውንና  100  የሚሆኑት  መቁሰላቸውን ”  ተናግሯል ።   ድርጅቱ  ድርጊቱን  በጽኑ  በማውገዝም ዓለም አቀፍ ማህበረሰብና የሰብዓዊ  መብት ድርጅቶች  በግድያው  እጃቸውን ያስገቡትን በሙሉ  ለፍርድ እንዲያቀርቡ ጥሪ አቅርበዋል ።     

በሰላማዊ ሰልፉ የተሳተፉት ኤርትራውያን ለአልጀዚራ  እንደተናገሩት ከማክሰኞ ዕለት ጀምሮ ለተካሄደው የተቃውሞ  ሰለፍ መነሻ  የኤርትራ  መንግሥት ዲያ በተባለ  የሙስሊም ማህበረሰብ ትምህርት  ቤት ውስጥ ሂጃብን መልበስንና  የሐይማኖት  ትምህርትን መሥጠት በመከልከሉ ነው ብለዋል ።    

በአስመራ ከተማ  3ሺህ ሙስሊሞችን ከሚያስተምረው ትምህርት ቤት የተነሳው የተቃውሞ ሰለፍ  ወደ የተለያዩ አካባቢዎች መዛመቱ  ፍጹም ተቃውሞ  በማይፈቀድባትና የሰብዓዊ መብት ጥሰት በሚካሄድባት  ኤርትራ ትልቅ  ትንግርት መሆኑ  አስተያያት  ሠጪዎች  እየተናገሩ ይገኛሉ ።                                                    

የኤርትራ መንግሥት የአል ደያ የእስልምና ትምህርት ቤትን የህዝብ ትምህርት  ቤት ለማድረግ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ  በስውዲን የምትገኘው የኤርትራውያን  ሰብዓዊ መብት ተሟጋች  ሞሮን እስጢፋኖስ  ለአልጀዚራ  ተናግራለች ።   

የአል ዲያ  ትምህርት  ቤት ፕሬዚደንት ሃጂ  ሙሳ  በፀጥታ ሃይሎች በቁጥጥር ሥር መዋል  በአሥመራ ከተማ የተካሄደውን  ሰላማዊ ሰልፍ  ይበልጥ እንዳባባሰው  ተገልጿል ።

በትምህርት ቤቱ ውስጥ  የገቡት  የኤርትራ የፀጥታ ሃይሎች ተማሪዎችን  ከመደብደባቸውም በላይ  በማዕከላዊ አስመራ  ሰላማዊ ሰልፍ ያካሄዱትን ዜጎች በሃይል  ለመበተን ተሞክሯል ።       

የኤርትራው ፕሬዚደንት ቃል አቀባይና የኤርትራ የኢንፎርሜሽን ሚንስትር  የማነ ገብረመስቀል የተቃውሞ ሰልፉን  በትዊተር ገጻቸው ያስተባባሉ ሲሆን በአንድ ትምህርት  ቤት  የተነሳ  ተቃውሞ በራሱ  ትልቅ  ሰበር ዜና መሆኑ  ያስገርማል  ብለዋል ።  

ሌላዋ  ነዋሪነቷ በእንግሊዝ ለንደን ከተማ የሆነው የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ሰላም ኪዳኔ እንደምትገልጸው  የኤርትራ መንግሥት  የዜጎችን  ሰብዓዊ መብት ለመጋፋት  የሚወስዳቸው  ሠይጣናዊ እርምጃዎች እጅግ ዘግናኝ ናቸው ብላላች ።          

ዜጎች የትኛውንም መንገድ  በመጠቀም  አደገኛ ሁኔታዎችን  በማለፍ  ጭምር ኤርትራውያን ወጣቶች  አገራቸውን በመልቀቅ ላይ ይገኛሉ በማለት ሰላም አስተያየቷን ለአልጀዚራ አስተያያቷን ገልጻለች ። ( ምንጭ: አልጀዚራ)